ሠራዊቱ የኢትዮዽያ ታሪካዊ ጠላቶች ተላላኪ በመሆን በባንዳነት በተሰለፈው ፅንፈኛ ቡድን ላይ ተከታትሎ እርምጃ በመውሰድ ሰላምን በዘላቂነት እያፀና መሆኑን የምስራቅ ዕዝ ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል መሀመድ ተሰማ ገለጹ፡፡
ሌተናል ጄኔራል መሀመድ ተሰማ፤ በሰሜን ጎጃም እና በአዊ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞኖች በግዳጅ ላይ የሚገኘውን ኮር የግዳጅ አፈጻጸም የመስክ ምልከታ አድርገዋል።
ከመስክ ምልከታቸውም በኋላ ከዞንና ከወረዳ አመራሮች እንዲሁም ሌሎች አመራሮች ጋር የተወያዩ ሲሆን በሰሜን አቸፈር ወረዳ ሊበን ከተማ በአንድ ክፍለ ጦር የስልጠና ማጠናቀቂያ ላይ በመገኘትም የስራ መመሪያና ስምሪት ሰጥተዋል።

ሌተናል ጄኔራል መሃመድ በዚሁ ወቅት ባደረጉት ንግግር፤ ሰራዊቱ የኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶች ተላላኪ በመሆን በባንዳነት የተሰለፈውን ፅንፈኛ ቡድን ተከታትሎ እርምጃ በመውሰድ ሰላምን በዘላቂነት እያፀና ይገኛል ብለዋል።
በተለያዩ አካባቢዎች በመሽሎክለክ ሕብረተሰቡን በማገትና በመዝረፍ ወንጀል የሚፈፅመውን ፅንፈኛ ቡድን ሰራዊቱ ከሕዝቡ ጋር በመተባበር ተከታትሎ እርምጃ እየወሰደ መሆኑን አንስተው፤ ይህም ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል።
የታሪካዊ ጠላቶችን ተልዕኮ በመቀበል በክህደት በዜጎች ላይ ወንጀል ለመፈፀም የሚንቀሳቀሰውን ፅንፈኛ ቡድን በየደረጃው የሚገኘው አመራር፣ ሕዝቡና የፀጥታ ሃይሉ በትብብር ሕግ የማስከበር ስራውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ አሳስበዋል።
ኢዜአ እንደዘገበው በኢትዮጵያ ሁሉም አካባቢዎች ሰላምን በማፅናትና የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶችን በማሳካት የኢትዮጵያን እድገትና ብልፅግና ማረጋገጥ የሁላችንም አደራ እና ሃላፊነት ሊሆን ይገባል ብለዋል።
የሰላምና የጀግንነት ተምሳሌት የሆነው የሀገር መከላከያ ሰራዊት ለኢትዮጵያ ክብርና ሉአላዊነት መከበር ከመቼውም ጊዜ በላይ በላቀ ዝግጁነት የሚገኝ መሆኑን ሌተናል ጄኔራል መሀመድ ተሰማ አረጋግጠዋል።
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ድረ-ገፅ
https://dfmc.mod.gov.et/
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ዩቲዩብ
https://youtube.com/@fdredefenseforce-9629?si=Av-sDKCopw1FfTW2
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ቴሌግራም
https://t.me/+E_EOiTY9eq85ODI0
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ፌስቡክ
https://www.facebook.com/fdredefense.official





