የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ ኢንጂነሪንግ ኮሌጅ በሀገረ መንግስት ምስረታ፣ በሀገራዊ ታሪካዊ እውነታዎች እንዲሁም በብሔራዊ ጥቅሞች እና ፍላጎቶች ላይ ለዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ ለሁለት ሳምንታት ሲሰጥ የቆየውን የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና አጠናቋል።
በማጠቃለያ መድረኩ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ወታደራዊ አማካሪና የተኩስ አመራር ኃላፊ ጄኔራል አለምሸት ደግፌ “ሀገር በሥነ ምግባር በተሞላ አዕምሮ፣ በድፍረት በተሞሉ ልቦች እና ለታሪክ ያላቸውን የኃላፊነት ክብደት በተረዱ ወታደሮች ይገነባል” ሲሉ ተናግረዋል።
ጄኔራል መኮንኑ ከ50 ዓመታት በላይ በወታደራዊ አገልግሎት ስለ ወታደራዊ ግዴታ እና የሞራል መሠረቶች ያገኙትን ልምድ እና ተሞክሮ ብሎም ግንዛቤ አካፍለዋል።

የመቻቻልን፣ የአንድነትን እና የባህል ማንነትን አስፈላጊነት እንደ ብሔራዊ አንድነት ቁልፍ ምሰሶዎች አድርጎ መውሰድ ለሀገር መንግስት ግንባታችን ፋይዳው ዘርፈ ብዙ ነው ሲሉም ገልፀዋል።
ጄኔራል አለምሸት ማህበራዊ ሚዲያ አሁን ላይ ራሱን ችሎ የጦር ሜዳ ነው፤ በግድየለሽነት እና በሀሰት የተሞሉ ልጥፎች በሺዎች የሚቆጠሩ ወታደሮችን ደህንነት አደጋ ሊጥሉ ስለሚችሉ የሀገርን ብሔራዊ ጥቅም እና ፍላጎት ለማስጠበቅ በዲሲፕሊን፣ በብልሃት እና በአርበኝነት መጠቀም እንደሚገባ አፅንኦት ሰጥተው መክረዋል።
የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ ኘሬዝዳንት ብርጋዲየር ጄኔራል ከበደ ረጋሳ በበኩላቸው በብሔራዊ ጥቅሞች እና ፍላጎቶች ላይ የመከላከያ ኃይላችን ጥንካሬው ተልዕኮውን በግልጽ መረዳቱ ፣ በሥነ ምግባር መታነፁ ብሎም ስለ ወቅታዊ የብሔራዊ ደህንነት እና አካባቢያዊ ስትራቴጂክ ሁኔታ ያለው እውቀቱ ነው ሲሉ ተናግረዋል።
የኢንጂነሪንግ ኮሌጅ ዋና ዳይሬክተር ኮሎኔል ኢዶሳ ቱፋ በኮሌጁ የተሰናዳው መድረክ በዋነኝነት ሰራዊቱ በፈተናዎች ሁሉ እየፀና ለሀገር ያለውን ፍቅር በደሙ እያረጋገጠ፤ የህዝብ አለኝታነቱን እንደሚያስቀጥል ለማስገንዘብ ያለመ ነው ሲሉ ገልፀዋል።
የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ ለጄኔራል አለምሸት ደግፌ በወታደራዊ አገልግሎት ዘመናቸው ለሀገራቸው ላበረከቱት የላቀ ወታደራዊ የአመራርነት ሚና ዩኒቨርሲቲው የህይወት ዘመን ጥልቅ አክብሮት እና እውቅናን የሚያሳይ ሽልማት አበርክቶላቸዋል።
በተጨማሪም በመከላከያ ዋር ኮሌጅ ምርምር ማዕከል የሃገር ውስጥ ደህንነት ምርምር ትምህርት ክፍል ኃላፊ ለሆኑት ፕሮፌሠር አየለ በኸሪ በግንዛቤ ማስጨበጫ መድረኩ ለሰጡት ትምህርት ከጄኔራል አለምሸት ደግፌ እጅ የእውቅና ሰርተፍኬት ተቀብለዋል። ዘገባው የዩኒቨርሲቲው የሠራዊት ሥነ ልቦና ግንባታ ነው
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ድረ-ገፅ
https://dfmc.mod.gov.et/
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ዩቲዩብ
https://youtube.com/@fdredefenseforce-9629?si=Av-sDKCopw1FfTW2
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ቴሌግራም
https://t.me/+E_EOiTY9eq85ODI0
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ፌስቡክ
https://www.facebook.com/fdredefense.official





