የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት መጋቢት 19 ቀን 2017 ዓ.ም
የመከላከያ ስፔሻላይዝድ ሪፈራል ሆስፒታል በይፋ ተመርቆ ሥራ ከጀመረበት ጊዜ ጀምሮ የሠራዊቱን የጤና አገልግሎት አሰጣጥ በማዘመን እና ከፍ ወዳለ ደረጃ በማሸጋገር ውጤታማ ስራ እየሰራ እንደሚገኝ የመከላከያ ሚኒስቴር ፋይናንስ ዘርፍ ሚኒስትር ዲኤታ ወይዘሮ ማርታ ሉዊጂ ተናግረዋል።
ሚኒስትር ዲኤታዋ ሆስፒታሉ ወጪ ቆጣቢ በሆነ መንገድ በየጊዜው የሚያስደምም ውጤት እያስመዘገበ ይቻላልን በተግባር እያረጋገጠ የሚገኝ ተቋም እንደሆነ ጠቁመው ለዚህም በቅርቡ ለሰራዊቱ የተደረገው የዳሌ መገጣጠሚያ አጥንት ቅየራ ህክምና አንዱ ማረጋገጫ እንደሆነም አረጋግጠዋል።ይህ ደግሞ በየደረጃው የሚገኝ አመራር ሙያተኛ እና ባለ ድርሻ አካላት በጋራ በመተባበር እና በመደጋገፍ በመስራታችሁ የተገኘ ውጤት ነው ልትመሰገኑ ይገባልም ብለዋል

የመከላከያ ጤና ዋና መምርያ ኃላፊ ሌተናል ጄኔራል ጥጋቡ ይልማ በበኩላቸው ሆስፒታሉ እንደ ሀገር እና እንደ ተቋም የተቀመጠውን የዘመናዊ የጤና አገልግሎት አሰጣጥ ግብ ሊያሳካ የሚችል ስራ መሰራቱን ተናግረዋል ።
በቀጣይም ሆስፒታሉን በዘመናዊ የህክምና መሳሪያዎች እና ሙያተኞች በማሟላት በአፍሪካ ውስጥ ተመራጭ እና ተወዳዳሪ የህክምና ማዕከል እንዲሆን የማድረጉ ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። አሁን ላይ የተሰራው የዳሌ መገጣጠሚያ ቅየራም ይህንን ተግባር የሚያረጋግጥ እንደሆነም አንስተዋል ።
በተጨማሪም ምንግዜም ስራዎች አመራሩ ችግር ፈች የሆኑ ውሳኔዎች እየሰጠ እና የጤና ሙያተኛው ደግሞ በከፍተኛ የሃላፊነት ስሜት መስራት ከተቻለ የማይቻል ነገር እንደሌለ ያረጋገጠ ተግባር ፈጽማችኋልና ተቋሙም ሀገርም ይኮራባችኋለች ነው ያሉት ጄኔራል መኮኑ።
የመከላከያ ስፔሻላይዝድ ሪፈራል ሆስፒታል ዋና አዛዥ ብርጋዴር ጄኔራል ሸዋዬ ኃይሌ ሆስፒታሉ በ2017 በጀት አመት በታቀደው እቅድ መሰረት ከመከላከያ የፋይናንስ ዘርፍ ጋር በመነጋገር አስፈላጊው በጀት እንዲፈቀድ በማድረግ ከ685 በላይ ዘመናዊ የህክምና መሳሪያዎችን ከውጭ ሀገር በማስገባት እና በማስገጠም ወደ ስራ መግባታቸውን ገልጸዋል ።
ከዚህ ጋር ተያይዞም 104 የሚሆኑ የመገጣጠሚያ አጥንት ጉዳት የደረሰባቸውን የሠራዊት አባላትን ተቀብለው ለ53 አባላት የተሳካ ህክምና መደረጉን ተናግረዋል። ታካሚዎቹም በመልካም ሁኔታ ላይ ይገኛሉ ለቀሩት ታካሚዎችም የዳሌ እና የመገጣጠሚያ አጥንት ቅየራ ህክምናው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አንስተዋል ።
ሆስፒታሉ የተሰጠውን ተልዕኮ በአግባቡ እንዲወጣ ድጋፍ እና ትብብር ላደረጉላቸው አካላት በሆስፒታሉ ለሚሠሩ ሙያተኞች እና ሠራተኞች ለባለ ድርሻ አካላት በሙሉ በሆስፒታሉ እና በራሳቸው ስም ምስጋና አቅርበዋል።
በኤሊያስ ከለለኝ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ዩቲዩብ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ቴሌግራም
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ፌስቡክ