የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ሚያዝያ 20 ቀን 2017 ዓ.ም
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር ክቡር ዶክተር ጌድዮን ጢሞቲዎስ በወቅታዊ ዓለም አቀፋዊ ፣ አህጉራዊ ፣ ቀጠናዊና ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ለከፍተኛ የመከላከያ ሠራዊቱ አመራሮች ማብራሪያ ሰጥተዋል።
“የመሀሉ ዘመን” በሚል ርዕስ ትንታኔ ያቀረቡት ሚኒስትሩ በሀገራችን የመጣውን ለውጥ ተከትሎ በተመዘገቡ ሁለንተናዊ ድሎች ሳንዘናጋ ለበለጠ ድል መትጋት ይገባል ብለዋል።ታላቁን የህዳሴ ግድብ በከፍተኛ ፈተናዎች ውስጥ ገንብተን በማጠናቀቅ ሀገርና ህዝብን አንገት ከማስደፋት ለማዳን የተቻለበትና የጠላቶቻችን የተቀናጀ ሴራ ያከሸፍንበት አንዱ ማሳያ ነው ሲሉ ተናግረዋል።
ሀገራዊ ኢኮኖሚያችን ፈተናዎችን በመቋቋም በከፍተኛ ሁኔታ ማደጉንም ዓለም አቀፍና ሀገራዊ መረጃዎችን በማጣቀስ አብራርተዋል።
ባለፉት ዓመታት ብዙ ሀገራት በዲፕሎማሲው መስክ በትብብር ለመስራት ፍቃደኝነታቸውን ማሳየታቸውንና ይህንን በጎ ዕድል በመጠቀም የብሄራዊ ጥቅማችን ለማሳካት ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝም ጠቁመዋል።
የሀገራችንን ብሄራዊ ጥቅም ለማረጋገጥና የባህር በር ተጠቃሚ ለመሆን ያቀረብነው ጥያቄ በዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ፍትሃዊ አጀንዳ ሆኖ መያዙንም ገልፀዋል።ተለዋዋጭና ኢ-ተገማች በሆነው ዓለም አቀፋዊና ቀጠናዊ እንቅስቃሴ ያለንን ሁለንተናዊ ዝግጁነት በማረጋገጥና የተለያዩ ስልቶችን በመንደፍ ተጋላጭነታችንን ለመቀነስ ስራዎች እየተሰሩ እንደሚገኝም ገልፀዋል።
በተከተልነው የሰላም ስምምነት የፀና ወታደራዊ ድል ተመዝግቧል ያሉት ዶክተር ጌድዮን ጢሞቲዎስ ፣ የሚያጋጥሙ ውስጣዊ ችግሮችን በሰላምና በይቅርታ በመፍታት በሀገርና በህዝብ ላይ የሚደርሰውን ጥፋት ለመቀነስ መንግስት እየወሰደው ያለው በሳል እርምጃ ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገቡንም ተናግረዋል።
የሰላምን ጥሪ ባለመቀበል በሀይል ጥቅማችንን እናስከብራለን በማለት የሞከሩ የጥፋት ሀይሎች በተከተሉት የተሳሳተ ትርክትና ፖለቲካ ህዝቡ አንቅሮ እንደተፋቸውም ገልፀዋል።
የመከላከያ ሠራዊቱ ከሌሎች የፀጥታ ሀይሎች ጋር በመሆን በፅንፈኞች ላይ በወሰደው እርምጃም ለሀገርና ለህዝብ ስጋት ከመሆን ወርደው የራሳቸውን ህልውና ለማቆየት እየተቸገሩ መምጣታቸውን አንስተዋል ።
ሠላምን ለማፅናትና ብልፅግናንን ለማረጋገጥ በቁርጠኝነት መስራት እንደሚገባ ገልፀው ጀግናው የመከላከያ ሠራዊታችንም ባስመዘገባቸው ድሎች ሳይኩራራ ለበለጠ ተልዕኮ ራሱን ማዘጋጀት ይገባዋል ብለዋል።
በውይይቱ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላን ጨምሮ ከፍተኛ የሠራዊቱ አመራሮች ተገኝተዋል።
በብዙአየሁ ተሾመ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ዩቲዩብ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ቴሌግራም
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ፌስቡክ