የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ግንቦት 16 ቀን 2017 ዓ.ም
የጦር ኃይሎች ምክትል ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ጀኔራል አበበዉ ታደሰ በልዩ ዘመቻዎች ዕዝ በስልጠና ላይ ለሚገኙት የሠራዊቱ አመራሮች በሃገራዊ እና ቀጠናዊ ጉዳዮችን ላይ ማብራሪያ ሰጥተዋል።
በማብራሪያቸውም አንዳንድ ሃገራት እና አካላት የራሳቸዉን ፍላጎት ለማሟላት የዉስጥ ባንዳዎችን በመጠቀም ኢትዮጵያዊያንን በተለያየ መንገድ በመከፋፈል እና በማበጣበጥ አቅማቸዉን እናዳክማለን ብለዉ ላይሳካላቸው ይደክማሉ ብለዋል፡፡
የጭንቅላታቸዉ ሃሳብ ደርቆ ለሆዳቸዉ ያደሩ ፅንፈኞችና አሸባሪዎች ደግሞ የስልጣን ጥማቸዉን ለማርካት ለስልጣን የሚያበቃ ሃሳብና አገር የሚለዉ እሳቤ ጠፍቶባቸዉ በጉልበት ስልጣን እናገኛለን ብለዉ ባንዳ ሆነው እንደሚለፉም አንስተዋል።
እኛ ደግሞ ብሔርም ሃይማኖትም የማይከፋፍለን የሃገራችን እድገት እና ከፍታ እንዲሁም የህዝባችን መለወጥ እና መበልፀግ ዓላማ አድርገን ጎጥን ሳይሆን ኢትዮጵያን የምናስቀድም ኢትዮጵያዊ ወታደሮች ነን ሲሉ አስገንዝበዋል።
ጀኔራል አበባው በአሁኑ ሰዓት ስልጣን የሚያዘዉ በሃሳብ የበላይነት እንጅ በጉልበት አይደለም፤ እኛ መነሻችንም መዳረሻችንም ህገ-መንግስቱ ነዉ። ይህንን መነሻ በማድረግም ህግ እና ህገ መንግስታዊ ስርዓቱን ለማስከበር አገራችን የሚመጥን በትጥቅም በሰዉ ሃይልም የተደራጀ ዘመናዊ ሠራዊት ተገንብቷል፤ እንደ ልዩ ዘመቻዎች ዕዝም በኢትዮጵያ ታሪክ ታይቶ የማይታወቅ በርካታ ኮማንዶ እና አየር ወለድ እስፔሻል ፎርስ መገንባት ተችሏል ብለዋል።
ከሀገራችን ብሔራዊ ጥቅም ጋር በተያያዘም የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስከበር በሰላም ከሚያምን
ከሁሉም ጋር በሰላማዊ መንገድ እንሰራለን፤ በጉልበት የሚመጣ ካለ ግን የሀገራችንን ብሔራዊ ጥቅም ለማስከበር ሙሉ ዝግጁነት አለን ሲሉ ተናግረዋል።
በመጨረሻም እኛ ታሪክ ያለን የታላቅ አገር ሠራዊት ነን ለቀጠናዉ ሰላም መስፈንም ትልቅ ድርሻ እና ሃፊነት አለብን ፤ ይህን መሰረት አድርገን ቀጠናዊ ትስስርን በማጠናከር እየሰራን ነዉ ያሉት የጦር ሃይሎች ምክትል ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ጀኔራል አበበዉ ታደሰ ብዛት ቁጥር ያለው ህዝብ ይዘን በሰላማዊ መንገድ የቀይ ባህርን የወደብ አማራጭ መጠቀም አለብን ማለታችንን እንደስተት ቆጠረዉት የሚንጫጩ እንዳሉም ጠቅሰዋል።
በምህረት ስመኝ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ዩቲዩብ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ቴሌግራም
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ፌስቡክ