የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ግንቦት 16 ቀን 2017 ዓ.ም
ከግንቦት 11/2017 ዓ.ም ጀምሮ ሲካሄድ የቆየው የአለም አቀፉ ወታደራዊ ስፖርት ካውንስል 80ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ተጠናቋል። በዚህ ጉባኤ ላይ ኢትዮጵያን የወከለው ልዑካን ቡድን ስሪላንካ የተጓዘበት ዋነኛ ምክንያት ሃገራችን የዚሁ ምክር ቤት አባል እንድትሆን ምክንያታዊ ሃሳቦችን አቅርቦ ለማሳመንና አባል ለማድረግ ሲሆን የኢትዮጵያ ጥያቄ ተቀባይነት አግኝቶ
በአለም አቀፉ ወታደራዊ ስፖርት ካውንስል 142ኛዋ አባል ሃገር ሆና ተመዝግባለች።
የመቻል ስፖርት ክለብ ሥራ አመራር ቦርድ ሠብሳቢ ዶክተር ሠይፉ ጌታሁን በመድረኩ የኢትዮጵያ ሠራዊት በተሠማራባቸው ግዳጆች ሁሉ አሸናፊ የሆነና ሃገራችን በገጠሟት ፈተናዎች ሁሉ በልበ ሙሉነት ከጥቃት እየተከላከለ ተከብራ እንድትኖር ያስቻለ የድል ሠራዊት መሆኑን አሥገንዝበዋል።
የመከላከያ ክለብ የሆነው መቻል ከክለብ አልፈው ሃገር ያስጠሩ እንደነ ባሻዬ ፈለቀ፣ ሻምበል አበበ ቢቂላ፣ ሻምበል ማሞ ወልዴ፣ ሻምበል ምሩፅ ይፍጠር እና ሌሎችንም ስመ ጥርና ገናና ስፖርተኞችን እያፈራ 80 ዓመታት የዘለቀ ሀገራዊ ታሪክ ያለው አንጋፋ ክለብ መሆኑንም በስሪላንካው የስፖርት ጉባኤ መድረክ ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ የሰው ዘር መገኛ እና ታላላቅ ገድሎች የተፈፀሙባት ታሪካዊት ሃገር መሆኗን ያወሱት ዶክተር ሠይፉ በጉባኤው እየተሳተፈ የሚገኘው ኮሚቴ ኢትዮጵያ የአለም አቀፉ ስፖርት ምክር አባል በመሆኗ ደስተኛ መሆናቸውንም ገልፀዋል።
ዶክተር ሰይፉ ኢትዮጵያ የስፖርት ካውንስል አባል ሀገር እንድትሆን በሃሳብ ለደገፉ ሃገራት በሙሉ፣ ለዓለም አቀፉ ወታደራዊ ስፖርት ምክር ቤት CISM እና ለአፍሪካ ወታደራዊ ስፖርት ምክር ቤት OSMA አመራሮች እንዲሁም ለቦርዱ አመራር አባላት ልባዊ ምስጋና አቅርበዋል።
ኢትዮጵያ በአለም ዓቀፍ የሠላም ማስከበር ተልዕኮ አፈፃፀም የረጅም አመታት ታሪክ ያላት ተወዳጅ ጠንካራና በችግሮች የማይንበረከክ ተመራጭ ዘመናዊ ሠራዊት መገንባት የቻለች ሀገር መሆኗም ተገልጿል።
በጉባኤው የተሳተፉ የተለያዩ ሀገራት ተወካዮች በስፖርቱ ዘርፍ ከኢትዮጵያ ጋር አብረው መሥራት በሚችሉባቸው ጉዳዮች ላይ ኮሚቴው ውይይት አድርጓል።
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ዩቲዩብ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ቴሌግራም
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ፌስቡክ
fdredefense.official