ሌተናል ጀነራል ይመር መኮንን
የኢፌዴሪ መከላከያ ሰራዊት ግንቦት 30 ቀን 2017 ዓ.ም
የመከላከያ አዛዥነትና ስታፍ ኮሌጅ በአጭር ኮርስ ያሰለጠናቸውን የክፍለ ጦር አመራሮችን አስመረቋል።
በምረቃው ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የመከላከያ ትምህርትና ስልጠና ሀላፊ ሌተናል ጀነራል ይመር መኮንን ባስተላለፉት መልዕክት ወቅታዊ ፣ ውስጣዊ ፣ ቀጠናዊና አካባቢያዊ ሁኔታዎችን የተረዱ ብቻ በሳይንሳዊ መልኩ የሚተነብዩ አመራሮችን ለማፍራት የኮሌጁ ሚና የላቀ መሆኑን ጠቅሰዋል።
አመራሮቹ በተግባራዊ ውጊያ የተፈተኑና የውጊያ ልምድ ያላቸው መሆኑን የጠቀሱት ሀላፊው ስልጠናው ተለዋዋጭ ወታደራዊ ሁኔታዎች እንዲገነዘቡ ያደረገ ተግባር ተኮር ስልጠና መሰጠቱ ፋይዳው የጎላ መሆኑንም ገልጸዋል።
መከላከያ የሀገራችንን ሰላም በዘላቂነት ለማስጠበቅ ዘመናዊ፣ ፕሮፌሽናልና ዲሲፒሊንድ የሆነ ሰራዊት ለመገንባት እያደረገ ያለው ጥረት ውጤታማ መሆኑን ማሳያ መሆኑንም ተናግረዋል።
የዘመናችን ውጊያዎች ውስብስብ ፣ ዘመናዊና አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን መጠቀም የሚጠይቁ መሆናቸውን የገለፁት ሀላፊው፣ ለዚህም ያልተቋረጠ ስልጠና ወሳኝ መሆኑንና ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑንም ገልፀዋል።
ተመራቂ ከፍተኛ መኮንኖቹ ያላቸውን የረጅም ጊዜ የውትድርናና የአመራር ልምድ ካገኙት ስልጠና ጋር በማዋሀድ አሀዶቻቸውን ማደራጀት ማብቃትና በተፈለገው ጊዜና ቦታ የሚሰጣቸውን ግዳጅ በመፈፀም ሀገራቸውን ማኩራት እንደሚኖርባቸውም አሳስበዋል።
በዝግጅቱ ላይ የመከላከያ የትምህርትና ስልጠና ምክትል ሀላፊ ለአመራር ስልጠና ሜጀር ጀነራል ሰለሞን ቦጋለን ጨምሮ ከፍተኛ የሰራዊቱ አመራሮችና የኮሌጁ ማህበረሰብ ተገኝተዋል።
በብዙአየሁ ተሾመ