ሌተናል ጄኔራል ብርሃኑ በቀለ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ግንቦት 30 ቀን 2017 ዓ.ም
የኢትዮጵያን ሉዓላዊነትና ክብሯን ጠብቆ ማሻገር የኛ ትውልድ ኃላፊነት ነው ሲሉ የሰሜን ምዕራብ ዕዝ ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ብርሃኑ በቀለ ተናገሩ።
ሌተናል ጄኔራል ብርሃኑ በቀለ በአንድ ኮር በስልጠና ላይ የሚገኙ የመቶና የጓድ አመራሮች የስልጠና ሂደትን በተመለከቱበት ወቅት ኢትዮጵያ በጀግኖች ልጆቿ ክብር መስዋዕትነት ክብሯ ተጠብቆ ዛሬ ላይ ደርሳለች በእኛ ትውልድም የአፍሪካዊያን ኩራትና የነፃነት ተምሳሌት ሆና ትቀጥላለችም ብለዋል።
ኮሩ ፅንፈኛውን ቡድን በመደምሰስ ተልዕኮውን በላቀ ጀግንነት የፈፀመ ነው ያሉት ሌተናል ጄኔራል ብርሃኑ በቀለ ሠራዊቱን በመምራት፣በማስተባበር ራሳችሁም ጭምር ተዋጊ በመሆን አኩሪ ገድል ፈፅሟችኋልም ብለዋል።
ሠራዊቱን በሁለንተናዊ መስክ ለማብቃት የቅርብ አመራሩ ድጋፍና ክትትል ከፍተኛውን ሚና ይጫወታል ያሉት አዛዡ ሌተናል ጄኔራል ብርሃኑ በቀለ ብቃት ያለው የመቶና የጓድ አመራር ለጠንካራ ሠራዊት ግንባታ መሠረት ስለመሆኑም ተናግረዋል።
ተቋማችን ለሠራዊት ግንባታ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራበት ይገኛል ያሉት ሌተናል ጄኔራል ብርሃኑ በቀለ ከዘመኑ ጋር እየዘመነና በቴክኖሎጂ አቅሙ እያደገ በመምጣቱ ለኢትዮጵያ ክብር የሚመጥናት የመከላከያ ኃይል በመገንባት ላይ ስለ መሆኑም ተናግረዋል።
በየደረጃውና በየተመደብንበት የስራ መስክ ውጤታማ ስንሆን የፕሮፌሽናል ሠራዊት ግንባታውን እውን እናደርጋለን ያሉት የሰሜን ምዕራብ ዕዝ አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ብርሃኑ በቀለ በስልጠና የሚፈጠር ሁለንተናዊ አቅም ለቀጣይ ተልዕኮ ስኬት የበለጠ የሚያዘጋጅ መሆኑን በመገንዘብ ለውጤታማነት መትጋት ይጠበቅባችኋል ሲሉም አሳስበዋል።
በአንዷለም ከፍያለው
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ድረ-ገፅ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ዩቲዩብ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ቴሌግራም
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ፌስቡክ