የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ሰኔ 03 ቀን 2017 ዓ.ም
በጠቅላይ መምሪያው የጠቅላላ አገልግሎት ዋና ዳይሬክቶሬት በተሠጠው ዝርዝር ሃላፊነቶች መሠረት ሠራዊቱንና ቤተሠቡን በፍትሃዊነት እያገለገለ እንደሚገኝ የዋና ዳይሬክቶሬቱ ዳይሬክተር ሜጄር ጄኔራል አብዱ ከድር ገለፁ።
አሠራርና መመሪያው በሚያዘው መሠረት የሠራዊቱን የመኖሪያ ቤትና የሥራ መገልገያ ቢሮዎችን ማመቻቸት ፣እንደ ውሃ መብራትና ሌሎች አገልግሎት መሥጫዎችን መከታተል እንደአሥፈላጊነቱ የመጠገንና ለአገልግሎት ምቹ የማድረግ ሥራዎች በክፍሉ እየተከናወነ ሥለመሆኑ አሥረድተዋል።
የካምፖችና ቤቶች አሥተዳደር ከቤት ዕደላና ከጥገና ሥራዎች ጋር በተያያዘ አሥፈላጊውን ክትትል እያደረገ ሥለመሆኑ የተናገሩት ሜጄር ጄኔራል አብዱ ከድር እየተጠናቀቀ ባለው የ2017 በጀት ዓመት ከአንድ ሺህ በላይ ቤቶች ለሠራዊት መታደላቸውንና የመኖሪያ ቤት እጥረትን ሊቀርፉ የሚችሉ በርካታ ቤቶች በካምፖች በተለይም ደግሞ በጎፋ ካምፕ እየተገነቡ መሆኑን ተናግረዋል።
ሠራዊቱንና ቤተሠቡን ከመደጎም አንፃር በመደብሮችና መዝናኛ ክበቦች አማካኝነት በርካታ ችግር ፈች ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑንም ገልፀዋል። በአነስተኛና ተመጣጣኝ በሆነ ዋጋ እንደ ዘይት ስኳር ፊኖ እና መሠል የሸቀጣሸቀጥ ፍጆታዎች ለሠራዊቱ ተደራሽ እንደሚሆኑና ክበቦች በአነስተኛ ዋጋ ለሠራዊቱ አሥፈላጊውን የምግብ አገልግሎት እንደሚሠጡም አንስተዋል።
የወተት ላሞች በማርባት በየካምፑ ለሠራዊቱ የወተት አቅርቦት ማከናወን፣ በጠቅላይ መምሪያው በሚገኘው ሀይቅ ዓሣ በማሥገር ለሠራዊቱ ክፍሎች ማድረስ፣ የዶሮ እርባታ በሠፊው መሣተፍ ፣እንቁላል ለተጠቃሚው ማድረስ እና መሠል ሥራዎች ላይ ትኩረት በማድረግ የሠራዊቱንና ቤተሠቡን ኑሮ መደጎም እየተቻለ መሆኑን እና ቀጣይ ይበልጥ ሥራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ሜጄር ጄኔራል አብዱ ከድር አረጋግጠዋል።
ዘጋቢ ውብሸት ቸኮል
ፎቶግራፍ ደጀኔ አሳይቶ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ድረ-ገፅ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ዩቲዩብ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ቴሌግራም
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ፌስቡክ