የሠራዊት አባላት
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ሰኔ 08 ቀን 2017 ዓ.ም
የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ደህንነትን እያረጋገጥንና ለግንባታው በተለያየ መልኩ አስተዋጽኦ እያደረገን ነው ሲሉ በቀጠናው የሚገኙ የምዕራብ ዕዝ ሕዳሴ ኮር የሠራዊት አባላት ገለፁ።
የመላው ኢትዮጵያውያን አሻራ ያረፈበት ታላቁ ሕዳሴ ግድብ መጠናቀቅ ደረጃ ላይ መድረሱ እንዳስደሰታቸውም ተናግረዋል።
በምዕራብ ዕዝ የሕዳሴ ኮር ሶስተኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን “ሕዳሴን በሕዳሴ ኮር” በሚል መሪ ሐሳብ በተለያዩ ዝግጅቶች በማክበር ላይ ይገኛል።
የሠራዊቱ አባላቱም ታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ጎብኝተዋል። በጉብኝታቸውም የመላው ኢትዮጵያውያን አሻራ ያረፈበት ታላቁ ሕዳሴ ግድብ ወደ መጠናቀቁ ደረጃ ደርሶ በመመልከታቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል።
የምዕራብ ዕዝ ምክትል አዛዥ ሜጀር ጄኔራል ሙላቱ ጀልዴ በጉብኝቱ ወቅት፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ወደ መጠናቀቁ ደረጃ ለመድረሱ መላው ኢትዮጵያውያን ያላሰለሰ ጥረት ማድረጋቸውን ተናግረዋል።
መከላከያ ሠራዊቱ የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ እውን እንዲሆን የግድቡን ደህንነት ከማስጠበቅ ጀምሮ የሚጠበቅባቸውን ሁሉ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን ኢዜአ ዘግቧል።
በምዕራብ ዕዝ ኮር አዛዥ ብርጋዲየር ጄኔራል አዘዘው መኮንን እንደገለጹት፤ ሠራዊቱ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ለማስጠበቅና ግዳጁን በብቃት ለመወጣት ከምን ጊዜውም በላይ ዝግጁ ነው።
ሕዳሴ ኮር የግድቡን አካባቢ ሰላምና ጸጥታ ለማስከበር እያደረገ ያለውን ተግባር በውጤታማነት እየተወጣ መሆኑን ጠቁመው፤ ይህንን ተግባሩን አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
ከምዕራብ ዕዝ ሌተናል ኮሎኔል ፍሰሃ ጥላሁን በበኩላቸው የታላቁ የህዳሴ ግድብ የመላው ኢትዮጵያውያን እስትንፋስ በመሆኑ ሠራዊቱ ሁሌም የአካባቢውን ሰላም በማስጠበቅ ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል።
ታላቁ የሕደሴ ግድብ አሁን የደረሰበት ደረጃ ላይ እንዲደርስ ሠራዊቱ አስፈላጊውን ሁሉ ማበርከቱን ጠቁመዋል። ዛሬ ለደረሰበት የመጠናቀቅ ደረጃ ደርሶ በመመልከታቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል።
ሌተናል ኮሎኔል ቴዎድሮስ ዘመነ እንዳሉትም፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የኢትዮጵያውያን የይቻላል መንፈስ ማሳያ ነው። ታላቁ ሕዳሴ ግድብ ለሀገር በረከት የመሆን ደረጃ ላይ በመድረሱ መደሰታቸውን ጨምረው ተናግረዋል።
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ድረ-ገፅ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ዩቲዩብ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ቴሌግራም
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ፌስቡክ