ሩሲያ ባዘጋጀችው የማርችንግ ባንድ ፌስቲቫል ላይ የሚሳተፈው የኢትዮጵያ መከላከያ ማርችንግ ባንድ ቡድን ዛሬ ወደ ሩሲያ እንደሚጓዝ የመከላከያ ሠራዊት ሥነ ልቦና ግንባታ ዋና ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ሜጀር ጄኔራል እንዳልካቸው ወልደኪዳን አሥታውቀዋል።
የመከላከያ ማርችንግ ባንድ ቡድን ለመጀመሪያ ጊዜ በዚሁ የማርችንግ ባንድ ፌስቲቫል የሚካፈለው ከሩሲያ በቀረበለት ጥሪ መሠረት መሆኑን የገለፁት ሜጄር ጄኔራል እንዳልካቸው ወልደኪዳን ቡድኑ ሃምሳ አባላትን የያዘ ሆኖ በዛሬው ምሽት ወደ ሩሲያ እንደሚጓዝም ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ በሩሲያ የማርችንግ ባንድ ፌስቲቫል ላይ መሳተፏ የሁለቱን ወዳጅ ሀገራት ግንኙነት ይበልጥ የሚያጠናክር እና ወታደራዊ የልምድ ልውውጥን ለማድረግ እንደሚያግዝም ገልፀዋል።
በዚሁ ፌስቲቫል ላይ የሚሳተፈው የመከላከያ ማርችንግ ባንድ ቡድን ከተጋባዥ የአፍሪካ ሀገራት ማርችንግ ባንዶች ጋርም የተሞክሮ እና የልምድ ልውውጦችን ለማድረግ መልካም አጋጣሚ እንደሚሆንም ሜጄር ጄኔራል እንዳልካቸው አሥገንዝበዋል።
የመከላከያ ማርችንግ ባንድ ቡድን በተለይ ባለፉት ሁለት ወራት ለፌስቲቫሉ ሊመጥን የሚችል ጠንካራ ልምምድ ሲያደርግ መቆየቱን ያነሱት ጄኔራል መኮንኑ በማርችንግ ባንዱ ብቻ ሙዚቃ መሥራት በሚያሥችል አግባብ በአዳዲስ ስራዎች ቡድኑ መዘጋጀቱንም አንስተዋል።
የተሻለ ብቃትና ሙያዊ አቅም ይዞ ወደ ሩሲያ የሚጓዘው ቡድን ከሁለት ሳምንታት በላይ የመቆየት ጊዜ እንዳለው የገለፁ ሲሆን ማርችንግ ባንዱ በፌስቲቫሉ መሳተፉ ከቡድኑ አልፎ ለመከላከያ ሠራዊት አንዱ የገፅታ ግንባታ በመሆኑ ሙያተኞች ወደ ሥፍራው የሚጓዙበትን ዓላማ በተገቢው አሳክተው እንዲመለሱ ሜጄር ጄኔራል እንዳልካቸው ወልደኪዳን አደራ ሠጥተዋል።
ዘጋቢ ውብሸት ቸኮል
ፎቶግራፍ አበረ አየነው