
የመከላከያ ሠራዊትን ወቅቱ ከደረሰበት ቴክኖሎጂ ጋር አስማምቶ የማይደፈር እንዲሆን ቀን ከሌሊት ለሰሩ አካላት ምስጋና ይገባል ሲሉ ፕሬዚዳንት ታየ አፅቀ ሥላሴ ገለጹ።
ፕሬዚዳንት ታየ አፅቀ ሥላሴ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶክተር) አቅራቢነት ከፍተኛ የጦር መኮንኖችን ሾመዋል።
በዚህ ወቅት ፕሬዚዳንቱ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ሹመቱ ከፍተኛ መኮንኖች ላሳዩት የሥራ ጥንካሬ፣ ታማኝነት እና ብርታት የተሰጠ መሆኑን አስረድተዋል።
ውትድርና ለሀገር ሉዓላዊነት እና ለሕዝብ ክብር ሕይወትን አሳልፎ ለመስጠት ቃል ኪዳን የሚገባበት ታላቅ ሙያ መሆኑንም ገልጸዋል።

የፅኑ ወታደር ቋንቋው ሀገርና ሕዝብን ማገልገል መሆኑን ጠቅሰው፤ የመከለከያ ሠራዊቱም በዚህ ረገድ ከመቼውም ጊዜ በላይ ዝግጁ መሆኑን ተናግረዋል።
የሠራዊቱ አሁናዊ ዝግጁነት የኢትዮጵያን ህልውና ለማይሹ አካላት ትልቅ መልዕክት የሚሰጥ መሆኑንም አብራርተዋል።
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት መልህቁ በሁሉም አግባብ ራስን መቻል እንዲሁም በቴክኖሎጂ እና ክህሎት ልቆ መገኘት መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል።
መከላከያ የኢትዮጵያን ህላዊ ለማወክ በጋሻ ጃግሬነት ለመሰለፍ የሚከጅሉ ቡድኖች ባለቡት አካባቢ ትልቅ መድህን ነው ብለዋል።
የመከላከያ ሠራዊትን ዘመኑ ከደረሰበት ቴክኖሎጂ አስማምቶ የማይደፈር እንዲሆን ቀን ከሌት ለሰሩ አካላትም ምስጋና አቅርበዋል።
የኢትዮጵያ መንገድ ሰላም፣ ልማት እና ብልጽግና መሆኑን የተናገሩት ፕሬዚዳንት ታየ አፅቀ ሥላሴ ፣ ይህን መንገድ ለማደናቀፍ የሚሹ አካላት ደግመው ደጋግመው ሊያስቡ ይገባል ሲሉም አስገንዝበዋል።