በአዲስ አበባ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን አዘጋጅነት በተካሄደው 29ኛው የፔፕሲ 30 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድር የመቻል አትሌቲክስ ቡድን በሁለቱም ፆታ የዋንጫ አሸናፊ ሆኗል።
መነሻ እና መድረሻው ሰሚት ለስላሳ ፋብሪካ በተደረገው የ30ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ውድድር በወንድ የመቻሉ አስር አለቃ አበባው ደሳለኝ አንደኛ በመወጣት የወርቅ ሜዳልያ ሲያሸንፍ ፣ በሴት የግል ተወዳዳሪ የሆነችው ረድኤት ዳንኤል አሸናፊ በመሆን የወርቅ ሜዳልያ ተሸልመዋል።

በውድድሩ ላይ ተገኝተው ለአሸናፊ አትሌቶች እና ክለቦች የዋንጫ እና የሜዳልያ ሽልማት የሠጡት የአዲስ አበባ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዘዳንት አትሌት መልካሙ ተገኝ ዶክተር ትዕዛዙ ሞሴ እና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ናቸው።
አጠቃላይ ድምር ውጤት በወንድ መቻል አትሌቲክስ ቡድን የዋንጫ አሸናፊ ሲሆን፣ ሁለተኛ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሶስተኛ ፌዴራል ማረሚያ ቤቶች ሆነዋል።
በሴት ድምር ውጤት መቻል የዋንጫ አሸናፊ ሲሆን ሁለተኛ ፌደራል ፖሊስ ሶስተኛ ደረጃ አልተሰጠም።
በአስር የአዲስ አባባ ከተማ ክለቦች መካከል በተደረገው 29ኛው የ30ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ውድድር በሁለቱም ፆታ በመቻል አትሌቶች የበላይነት ተጠናቋል።

መቻል አትሌቲክስ ቡድን ለሀገራችን ስፖርት እያደረገ ያለው ድጋፍ ከፍተኛ ነው ያሉት የአዲስ አበባ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዘዳንት አትሌት መልካሙ ተገኝ ይህንን የክለቡን ጥንካሬ ማስቀጠል አለበት ብለዋል።
አትሌት መልካሙ እንዳሉት ከመቻል ጋር በርካታ ስራዎችን እየሰራን እንገኛለን መቻል ማለት ታላላቅ አትሌቶችን ያፈራ እና የሀገር ባለውለታ በመሆኑ በቀጣይ ወደቀደመ ስምና ታሪኩ እንዲመልስ አስፈላጊውን ድጋፍ እናደርገለን በማለት ተናግረዋል።
በውድድሩ የመቻሎቹ አሰልጣኝ ሻምበል አዱኛ ቶላ እና ሻለቃ ባሻ ተስፋዬ ቦጋለ ኮከብ አሰልጣኝ በመባል የገንዘብ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።





