በደቡብ ሱዳን የሴክተር ኢስት አዛዥ ብርጋዲየር ጀኔራል ራዛቅ አህመድ የ2018 ዓ.ም የዘመን መለወጫ በዓልን በደቡብ ሱዳን ቦር ከሚገኘው የ20ኛ ሞተራይዝድ ሰላም አስከባሪ ሻለቃ ጋር አክብረዋል።
ብርጋዲየር ጀነራል ራዛቅ አህመድ፤ ኢትዮጵያ ከአለም ሃገራት ከምትለይባቸው በርካታ ዘመን ተሻጋሪ አኩሪ ታሪኮቿ ውስጥ የሰው ዘር መገኛና የራሷ የዘመን አቆጣጠር ቀመር እንዲሁም ፊደልን ቀርፃ መጠቀሟ ነው ብለዋል።
ኢትዮጵያ አስደናቂ ባህል ያላት ድንቅ ምድር መሆኗን የጠቀሱት ብርጋዲየር ጀነራል ራዛቅ አህመድ በተለይ በሰራዊቱ ውስጥ የሚታየው የራስንም የሌሎችንም ባህል የማክበር ጥሩ ስነ-ምግባርን አጠናክሮ ከማስቀጠል ባሻገር እንደ ወታደር የኢትዮጵያ ሰላም አስከባሪ ሰራዊት በውስጣቸው ያለው ጓዳዊነት ከራስ ባለፈ ለሌሎች ሃገራት ሰራዊቶች አርአያ መሆን የሚችል ነው ብለዋል።
አዲሱን የዘመን መለወጫ በዓል ስታከብሩ ከዩናሚስ የተሰጣችሁን ዋነኛ ተልዕኮ በጀመራችሁት በተግባር እየታየ ባለው ውጤት ልክ አጠናክራችሁ በመቀጠል በተለይ የሰላም ግንባታ ላይ ዩናሚስ በቀጠናው እንዲመጣ በሚፈለገው ልክ ለመስራት መትጋት ይኖርባችኋል በማለት አሳስበዋል።
የ20ኛ ሞተራይዝድ ሰላም አስከባሪ ሻለቃ አዛዥ ኮሎኔል ሰጥየ አራጌ በበኩላቸው የኢትዮጵያ ሰላም አስከባሪ ሰራዊት በአለም ሰላም ማስከበር ሂደት ውስጥ ያለውን ለዘመናት የቆየ ስምና ዝናን አስጠብቀን ለመቆየትና ለአለም ሰላም ባለን ቁርጠኝነት ልክ በአዲሱ ዘመን በተሻለ ውጤት የነበረውን ውጤት ለማስቀጠል እንሰራለን በማለት ተናግረዋል።
ዘጋቢ አንዋር ሁሴን
ፎቶ ግራፍ መብርሂት ገብረሚካኢል