የአሜሪካ የአፍሪካ ዕዝ (AFRICOM) ከኢትዮጵያ ብሔራዊ መከላከያ ሠራዊት ጋር በመተባበር ለቀናት ሲያካሂድ የቆየው የአፍሪካ የሎጂስቲክስና የኮሙኒኬሽን ሲምፖዚየም በዛሬው ዕለት ተጠናቋል።
በሲምፖዚየሙ የመዝጊያ ሥነ-ሥርዓት ላይ የተገኙት የትራንስፖርትና ሎጀስቲክ ሚኒስትር ዶክተር አለሙ ስሜ፣ በታሪክ ውስጥ የሀገራት እድገትና ተፅዕኖ የተወሰነው በኢኮኖሚያቸው ጥንካሬ ወይም በጦር ኃይላቸው መጠን ብቻ ሳይሆን፣ በሎጂስቲክስ ሥርዓታቸው ውጤታማነትና በኮሙኒኬሽን አቅማቸው ላይ መሆኑን ገልጸዋል።

በዘመናዊው ዓለም ፍጥነት፣ ትክክለኛነት፣ አስተማማኝነትና አብሮ የመሥራት ብቃት ወሳኝ ጥቅሞች መሆናቸውን ገልፀው ፣ ሎጂስቲክስ አንድ ሀገር ራሷን የምታስቀጥልበትን፣ ሀብቷን የምታንቀሳቅስበትን፣ ተፅዕኖዋን የምታስፋፋበትንና በችግር ጊዜ ጽናቷን የምትጠብቅበትን አቅም የሚወስን መሆኑን ተናግረዋል።
ኮሙኒዩኬሽን ደግሞ መረጃን ለመሰብሰብ፣ ቅንጅትን ለማስቀጠል፣ ውሳኔን ለመደገፍና የጋራ ጥረትን ለማረጋገጥ መሠረታዊ ሚና እንዳለው አስረድተዋል።
እነዚህ ሁለት ዘርፎች በአንድነት ለሀገራዊ ሀይል ዋነኛ መሠረቶች መካከል እንደሚገኙ የገለጹት ሚንስትሩ፣ ጠንካራ የሎጂስቲክስ አውታርና አስተማማኝ የኮሙኒዩኬሽን ሥርዓት ከሌለ ማንኛውም ሀገር ሉዓላዊነቷን መጠበቅ፣ መረጋጋቷን ማስጠበቅ ወይም ብልጽግናዋን ማረጋገጥ እንደማትችል ጠቁመዋል።

አህጉራችን እየተጋፈጠች ያለችው የደህንነት ተግዳሮቶች እየተወሳሰቡ መምጣታቸውን በመግለጽም፣ የትጥቅ ግጭቶች፣ የሳይበር ጥቃቶች፣ የተፈጥሮ አደጋዎች፣ በአቅርቦት ሰንሰለት የሚፈጠሩ መቋረጦች፣ ወረርሽኞችና ድንበር ተሻጋሪ ወንጀሎች በጋራ ለመከላከል ሎጂስቲክስና ኮምኒዩኬሽን ሚና ማጠናከር ይገባል ብለዋል።
የአፍሪካ ደህንነትና ብልጽግና ትብብርን በማጠናከር፣ ፈጠራን በማበረታታት፣ አብሮ የመሥራት አቅምን በማሳደግ፣ እውቀትን በመጋራትና የጋራ አቅምን በመገንባት ላይ እንደሚመሰረት ጠቁመው፣ አፍሪካ አምራች የሰው ኃይል፣ የተፈጥሮ ሀብት፣ እያደጉ ያሉ ገበያዎችና ሰፊ የእድገት ዕድሎች እንዳሏት ገልጸዋል።
በተቋማት ላይ በመዋዕለ ንዋይ በማፍሰስና የቴክኖሎጂ ለውጥን በመቀበል ለዘላቂ ሰላም፣ ደህንነትና ብልጽግና ጠንካራ መሠረት መጣል እንደሚቻል ገልጸው፣ ኢትዮጵያም ለእነዚህ ዓላማዎች በፅናትና በቁርጠኝነት እየሰራች መሆኗን አረጋግጠዋል።

በዝግጅቱ ላይ በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ፣ የሎጂስቲክስ ዋና መምሪያ ኃላፊ ሌተናል ጀነራል አብዱራህማን እስማኤልን ጨምሮ የአፍሪኮም ከፍተኛ ወታደራዊ አመራሮች ተገኝተዋል።
ዘጋቢ ብዙአየሁ ተሾመ
ፎቶግራፍ ተሰማ ኡርጌሳ
