በአፍሪካ ሎጂስቲክስና ኮሙኒዩኬሽን ሲምፖዚየም መክፈቻ ላይ ንግግር ያደረጉት በአፍሪካ የአሜሪካ ዕዝ (አፍሪኮም) አዛዥ ጄኔራል ዳግቪን አንደርሰን፦ ሎጂስቲክስና ኮሙኒዩኬሽን ለዘመናዊ ወታደራዊ ዘመቻዎች የማይተካ አቅም መሆናቸውን ገልጸው፣ የአፍሪካ ሀገራት በእነዚህ ዘርፎች ላይ ተቀናጅተው መስራት እንደሚገባቸው ተናግረዋል።
ሎጂስቲክስ እና ኮሙኒዩኬሽንን በአንድ መድረክ ያሰባሰበው ይህ ሲምፖዚየም የመጀመሪያው ቢሆንም፣ ሁለቱም ዘርፎች ለወታደራዊ ተልዕኮ ስኬት የማይነጣጠሉ መሆናቸውን አመላክተዋል።

ሎጂስቲክስና የዘላቂ ድጋፍ ሥርዓቶች ብዙ ጊዜ ተገቢውን ትኩረትና ኢንቨስትመንት እንደማያገኙ ጠቁመው፣ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን መግዛት ብቻ በቂ እንዳልሆነ፣ እነዚህን ለማቆየት፣ ለመጠገንና ወደ ተፈለገው የተግባር ስፍራ ለማድረስ የሚያስችል ጠንካራ የሎጂስቲክስ ሥርዓት መኖሩ ወሳኝ መሆኑን አስረድተዋል።
ጄኔራል አንደርሰን አፍሪካ በአሁኑ ወቅት የሽብርተኝነት፣ የሕገ-ወጥ ማዕድን ማውጣት፣ የሕገ-ወጥ ዓሣ ማጥመድ፣ የሰው ዝውውርና የአደንዛዥ ዕፅ ዝውውርን ጨምሮ በርካታ የፀጥታ ተግዳሮቶችን እየተጋፈጠች መሆኗን ገልጸው፣ እነዚህን ችግሮች ለመቋቋም የሀገራት ትብብር፣ የመረጃ ልውውጥና የሎጂስቲክስ ቅንጅት ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል።

በተጨማሪም የዓለም ወቅታዊ የጦርነት ባህሪ በፍጥነት እየተቀየረ መሆኑን በመጥቀስ፣ ድሮኖች፣ ዲጂታል ኮሙኒዩኬሽንና የሳተላይት ቴክኖሎጂዎች አዲስ የደህንነት እውነታን እየፈጠሩ መሆናቸውን አስረድተው፣ የአፍሪካ ሀገራትም ከእነዚህ ለውጦች ጋር በመራመድ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በብቃት መጠቀም እንደሚገባቸው አመልክተዋል።
የደህንነትና የኢኮኖሚ ልማት የተሳሰሩ ጉዳዮች መሆናቸውን ያነሱት ጄኔራሉ፣ ከንግድና ከኢንዱስትሪ ተቋማት ጋር የሚደረግ ትብብር የቴክኖሎጂ ሽግግርን በማፋጠን ለሀገራዊ መከላከያና ፀጥታ አቅም መጠናከር ጉልህ አስተዋፅኦ እንደሚያበረክት ገልጸዋል።

ሎጂስቲክስ የቁሳቁስ አቅርቦት ብቻ ሳይሆን ከሕክምና ድጋፍ፣ ከጥገና እና ከወታደራዊ ዝግጁነት ጋር በቀጥታ የተያያዘ መሆኑን ጠቅሰው፣ ለረጅም ጊዜ የሚዘልቅ የመከላከያ አቅም ለመገንባት በሎጂስቲክስና በዘላቂ ድጋፍ ሥርዓቶች ላይ የሚደረግ ኢንቨስትመንት አስፈላጊ መሆኑን አስገንዝበዋል።
በመጨረሻም የኢትዮጵያ አየር መንገድን እንደ ስኬታማ ምሳሌ በማንሳት፣ ተቋሙ ዛሬ የአፍሪካ ትልቁ የአየር መንገድ ሊሆን የቻለው በሎጂስቲክስ፣ በጥገና፣ በሰው ኃይል ልማትና በዘላቂ ድጋፍ ሥርዓት ላይ በተደረገ የረጅም ጊዜ ኢንቨስትመንት መሆኑን ገልጸዋል።
የወደፊቱን የፀጥታ ተግዳሮቶችን ለመቋቋም የአፍሪካ ሀገራት በሎጂስቲክስ፣ በኮሙኒዩኬሽን፣ በፈጠራ እና በጋራ ትብብር ላይ ትኩረት በማድረግ ዘላቂ የመከላከያ አቅማቸውን ማጠናከር እንዳለባቸው ጥሪ አቅርበዋል።

የ2026 የአፍሪካ ሎጂስቲክስና ኮሙኒዩኬሽን ሲምፖዚየም እስከመጭው አርብ በተለያዩ ዝግጅቶች ይቀጥላል።
ዘጋቢ ብዙአየሁ ተሾመ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ድረ-ገፅ
