የ2026 የአፍሪካ ሎጂስቲክስና ኮሙኒዩኬሽን ሲምፖዚየም በይፋ ተከፍቷል። በዝግጅቱ ላይ በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሰደር ኤርቪን ማሲንጋ፣ የአሜሪካ የአፍሪካ ዕዝ አዛዥ (አፍሪኮም) ጀነራል ዳግላስ አንደርሰን፣ የመከላከያ ሎጂስቲክስ ዋና መምሪያ ሀላፊ ሌተናል ጀነራል አብዱራማን እስማኤልን ጨምሮ ከአርባ የአፍሪካ ሀገራት የተውጣጡ ተወካዮችና ሀያ ስድስት ዓለም አቀፍ ኢንዱስትሪ ተወካዮች ተገኝተዋል።

ዝግጅቱን በይፋ ከፍተው ንግግር ያቀረቡት የመከላከያ ሚኒስቴር ሚኒስትር ኢንጅነር አይሻ መሃመድ፣ አዲስ አበባን የሲምፖዚየሙ አስተናጋጅ ከተማ አድርጎ ለመምረጥ የተወሰነው ውሳኔ በኢትዮጵያና በአሜሪካ መካከል እያደገ የመጣውን የጋራ መተማመንና የስትራቴጂክ አጋርነት የሚያሳይ መሆኑን ገልጸዋል።
በተለይም በዲፕሎማሲና በወታደራዊ ትብብር ዘርፍ የሁለቱ አገራት ግንኙነት ወደ ከፍተኛ ስትራቴጂያዊ ደረጃ መሸጋገሩን የገለፁት ሚኒስትሯ፣ በኢትዮጵያ ላይ ለተጣለው እምነትና አመኔታ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
ሲምፖዚየሙ ከቴክኒካዊ ውይይቶች ባሻገር አጋርነትን የሚያጠናክር፣ ምርጥ ተሞክሮዎችን የሚያጋራ እና በመላው አፍሪካ ብቁ፣ የተሳሰሩና ለወደፊቱ ዝግጁ የሆኑ ተቋማትን ለመገንባት የጋራ ቁርጠኝነትን የሚያጠናክር መድረክ መሆኑንም አስገንዝበዋል።

እንዲሁም በትብብርና በፈጠራ አማካኝነት የዝግጁነት አቅምን ማሳደግ፣ በአፍሪካ አገራት የመከላከያ ኃይሎች መካከል የተቀናጀ አሠራርን ማጠናከር እና ለአህጉሪቱ ሰላም፣ ደህንነትና ዘላቂ ልማት የሚያበረክተውን አስተዋፅኦ የበለጠ ማጎልበት የሲምፖዚየሙ ዋና ዓላማ መሆኑን ገልጸዋል።

በመጨረሻም ተሳታፊዎች የዛሬን ተግዳሮቶች ብቻ ሳይሆን አፍሪካ ለወደፊቱ የምትፈልጋቸውን ስትራቴጂያዊ አቅሞች በጋራ እንዲገነቡ ጥሪ በማቅረብ፣ ለሲምፖዚየሙ የተሳካ ውይይትና ውጤታማ ቆይታ በመመኘት የ2026 የአፍሪካ ሎጂስቲክስና ኮሙኒዩኬሽን ሲምፖዚየምን በይፋ ከፍተዋል።

ዘጋቢ ብዙአየሁ ተሾመ
ፎቶግራፍ ተሰማ ኡርጌሳ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ድረ-ገፅ
https://dfmc.mod.gov.et/
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ዩቲዩብ
https://youtube.com/@fdredefenseforce-9629?si=Av-sDKCopw1FfTW2
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ቴሌግራም
https://t.me/+E_EOiTY9eq85ODI0
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ፌስቡክ
https://www.facebook.com/fdredefense.official
