የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ሰኔ 28 ቀን 2017 ዓ.ም
የመከላከያ ሠራዊቱን ፕሮፌሽናል በማድረግና በማዘመን በቀጣይ ሊከሰቱ የሚችሉ ስጋቶችን ከሩቅ የማስቀረትና ብሄራዊ አደጋ ቢከሰት በአስተማማኝ ሁኔታ መቀልበስ የሚችል አቅም ያለው ሠራዊት መገንባቱን የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ክቡር ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ ገልፀዋል።
የመከላከያ አዛዥነትና ስታፍ ኮሌጅ ለ15ኛ ጊዜ በመደበኛ ኮርስ ያሰለጠናቸውን ከፍተኛ መኮንኖች አስመርቋል።
በምረቃው ስነ-ስርዓት ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የጦር ሀይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ክቡር ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ ለተመራቂዎቹ ሰርተ-ፊኬት ከሰጡ በኋላ ባስተላለፉት መልዕክት፦ በሁለንተናዊ ዘርፉ የተለወጠ ፣ የወታደራዊ ስልትና ጥበብ የተላበሰና ኢትዮጵያን የሚመጥን የሀገር መከላከያ የመገንባት ጥረቱ በተሳካ ሁኔታ እየተከናወነ እንደሚገኝ ገልፀዋል።
ለሠራዊቱ የተሰጠው ሁለንተናዊ የአቅም ግንባታ ትኩረት ለተቋማዊ ዕድገታችን መሠረት ሆኖ መቀጠሉን ያወሱት ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ የተቋሙን ጠንካራ የትምህርትና የስልጠና ማዕከላትን የመገንባትና የማጠናከር ተግባሩ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ጠቁመዋል።
በቀጣይም የአገራችንን ሰላምና ደህንነት ለመጠበቅ በሰው ሀብት ግንባታ መስኩ በትኩረት እንደሚሰራም ተናግረዋል።
ተመራቂ ከፍተኛ መኮንኖቹ በኮሌጁ ባገኙት እውቀት ፣ ክህሎትና አስተሳሰብ በሚሰማሩባቸው ክፍሎችም በመተግበር በአርአያነት እንዲመሩ አሳስበዋል።
ኮሌጁ እያስተማራቸው ከሚገኙ የወዳጅ ሀገር ከፍተኛ መኮንኖች የሀገራችንን ወታደራዊ ዲፕሎማሲ ለማሻሻልና የህዝባችንን ባህል ለማስተዋወቅ ያላቸው ሚና ከፍተኛ በመሆኑ ተጠናክሮ መቀጠል እንደሚኖርበትም ገልፀዋል።
ኮሌጁ ከሀገራችን ከፍተኛ መኮንኖች በተጨማሪ ከሰባት የአፍሪካ ሀገራት የተውጣጡ አስራ ሶስት ከፍተኛ መኮንኖችም አስመርቋል።
በምረቃው ስነ ስርዓት ላይ ከፍተኛ የሠራዊቱ አመራሮች ፣ ዲፕሎማቶች ፣ የመንግስት የስራ ሀላፊዎች ፣ ወታደራዊ አታሼዎች ፣ የተመራቂ ቤተሰቦችና የኮሌጁ ማህበረሰብ ተገኝተዋል።
ዘጋቢ ብዙአየሁ ተሾመ





