የመከላከያ ሳይበር ዋና ዳይሬክቶሬት የ2017 በጀት ዓመት እቅድ አፈፃፀም አሥመልክቶ ባደረገው ውይይት ከተቋሙ የተሰጠውን የሳይበር ደህንነት የማረጋገጥ ተልዕኮ መፈፀም የሚችል የመከላከያ ሳይበር እየተገነባ እንደሚገኝ የመከላከያ ሳይበር ዋና ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ብርጋዲየር ጄኔራል ደረጀ ደመቀ ተናግረዋል፡፡
በበጀት ዓመቱ በሳይበር ደህንነት ዘርፈ ብዙ የአቅም ግንባታ ስራዎችን ማከናወን መቻሉ፣ የእውቀትና የቴክኖሎጂ ሽግግር በማረጋገጥ አመርቂ ስራና ውጤት የተመዘገበበት ዓመት መሆኑን እና አመራሩና አባላቱ የተሰጣቸውን ተልዕኮ መሰረት ያደረገ የሙያና የአመራር ስልጠና ያገኙበትና የመፈፀም አቅማቸውን ከፍ ማድረግ የቻሉበት እንደሆነ አረጋግጠዋል፡፡
ዓለምአቀፋዊና አገራዊ የሳይበር ደህንነት ማዕቀፎችና አሰራሮችን መሰረት በማድረግ የመከላከያ ሳይበር በአሰራር ስርዓትና ሂደት እንዲታገዝ ከማድረግ አኳያ የመከላከያ የሳይበር ደህንነት ፖሊሲ ሰነድ ታይቶና ፀድቆ ፖሊሲው በሁሉም ክፍሎች ተግባራዊ እንዲሆን በበላይ አካል አቅጣጫ የተሰጠበት መሆኑ ተመላክቷል።
የሳይበር ጥቃት ተጋላጭነትና ስጋትን፣ ምርጥ ልሞዶችና ተሞክሮዎችን መሰረት በማድረግ በተቋም ደረጃ የሳይበር ደህንነት የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ለበርካታ የሠራዊት አመራርና አባላት ተደራሽ ማድረግ የተቻለበት አመት እንደሆነ ታይቷል።
ከኃይሎች፣ ከእዞችና ከዋና ዳይሬክቶሬቱ ለተውጣጡ ሙያተኞች የመሰረታዊ የሳይበር ደህንነት ስልጠና ተሰጥቶ በሰርተ-ፊኬት ማስመረቅ መቻሉን በበጀት አመቱ ከተገኙ ስኬቶች አንዱ እንደሆነ ተገልጿል፡፡
የአውታረ መረብ ደህንነት የስራ ሂደት ሞኒተር ለማድረግና ወደ ተጨባጭ ስራዎች ለመግባት የሚያስችሉ የሀርድዌርና የሶፍትዌር የዝግጅት ስራዎች እየተደረጉ ያሉበትና በራስ ሙያተኞች አቅም የተሰሩ የተለያዩ የደህንነት ሶፍትዌሮች በመጠናቀቅ ላይ እንደሚገኙ ብርጋዲዬር ጄኔራል ደረጀ ደመቀ ገልፀዋል፡፡ መረጃው የመከላከያ ሳይበር ዋና ዳይሬክቶሬት ፅህፈት ቤት ነው





