ሌተናል ጄነራል ይልማ መርዳሳ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ሰኔ 17 ቀን 2017 ዓ.ም
የኢፌዴሪ አየር ኃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጄነራል ይልማ መርዳሳ የL 39 አውሮፕላን በረራ ስልጠናን አጠናቀው ወደ ቀጣዩ የተዋጊ ጄት በረራ ስልጠና ያለፉትን ሲኒዬር ካዴት አያንቱ ካሳን እና ሲኒዬር ካዴት ሀዊ ግርማን በአየር ኃይል በረራ ትምህርት ቤት አበረታትተዋል።
ሌተናል ጄነራል ይልማ መርዳሳ በአንድ ጊዜ ሁለት ሴት አብራሪዎች ከ L 39 አውሮፕላን ወደ ተዋጊ ጄት የበረራ ስልጠና ማለፋቸው በተቋሙ ታሪክ የመጀመሪያ እንደሆነ ጠቅሰው ይህም አየር ኃይላችን በተለይም ከሪፎርሙ ወዲህ በአብራሪነት ሙያ ምንም የሴት ተሳትፎ ያልነበረውን የተቋሙን መዋቅር በመቀየር ሴት ወታደሮችን ወደ ዘርፉ ማምጣት ብቻ ሳይሆን እስከ ተዋጊ ጄት የበረራ ስልጠና ድረስ ለማብቃት መቻሉ በራሱ ማሳያ መሆኑን ተናግረዋል።
ሁለቱ ሴት በራሪዎቻችንም ወደ ተዋጊ ጄት የበረራ ስልጠና ሲሸጋገሩ ሙያዊ አቅማቸውን ለዚህ ወሳኝ ስልጠና በሚመጥን ደረጃ ልክ ማሳደግ እንደሚገባም ሌተናል ጄነራል ይልማ መርዳሳ አያይዘው ገልፀዋል።
የአየር ኃይል በረራ ትምህርት ቤት አዛዥ ኮሎነል ጃምቦ አዛገ ትምህርት ቤቱ ተልዕኮው ከሁሉም የሀገሪቱ አከባቢዎች ተመልምለው መስፈርቱን በማሟላት ወደ በረራ ስልጠና ለሚገቡ ሰልጣኞች በተግባር እና ቲዮሪ የተደገፈ ስልጠናን በመስጠት ለተቋሙ ግዳጅ ዝግጁ ማድረግ መሆኑና በአሁን ወቅትም በአዲስ መዋቅራዊ አደረጃጀት በዘመኑ ቴክኖሎጂም ጭምር ታግዞ የበረራ ስልጠናውን በተሻለ ቁመና እያሳደገ መሆኑንም ጠቁመዋል።
በአቭዬሽን ሙያ መስክ እስከ ተዋጊ ጄት የበረራ ስልጠና ድረስ የመግባታቸው ትልቁ ምስጢር በአላማ ቁርጠኝነት እንዲሁም ጠንክሮ ከመስራት የሚመነጭ ውጤት መሆኑን ያወሱትና ቀጣይ ግባቸውም በዚህ ሙያ ከፍ ባለ ደረጃ ሀገራቸውን ብሎም ተቋሙን ማገልገል እንደሆነ ያስታወቁት ሲኒዬር ካዴት አያንቱ ካሳ እና ሲኒዬር ካዴት ሀዊ ግርማ ናቸው።
ዘጋቢ ፍቅሬ በቀለ
ፎቶግራፍ አብዱራህማን ሱልጣን
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ድረ-ገፅ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ዩቲዩብ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ቴሌግራም
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ፌስቡክ





