የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት መጋቢት 30 ቀን 2017 ዓ.ም
የመከላከያ ሚኒስቴር የ2017 ዓ.ም የዘጠኝ ወራት የእቅድ አፈፃፀም ውይይት አድርጓል። የሥራ አፈፃፀም ሪፖርቱን ያቀረቡት የሚኒስቴሩ እቅድ እና ሪፖርት ዝግጅት ክትትል ዳይሬክተር ኮሎኔል ፈይሳ ታደሰ በአንዳንድ ክፍሎች ላይ በስራ ሂደት እንቅስቃሴ ውስጥ ካጋጠሙ ችግሮች እና ከታዩ ክፍተቶች ውጭ ሁሉም ፈፃሚ አካላት ስራቸውን በትጋት በመፈፀማቸው አበረታች ውጤት መገኘቱን ተናግረዋል።
ሠራዊቱን ከአዳዲስ ቴክኖሎጅ ጋር በማዋሀድ በአስተማማኝ መልኩ ሠላምን እንዲጠብቅ በማድረግ በኩል ከፍተኛ ተግባራት መከናወኑን አንስተዋል። የኢንዱስትሪዎችን አቅም በማሳደግ፣ ወታደራዊ ዲፕሎማሲውን ከፍ በማድረግ፣ የሰው ሀብት አቅምን በማደራጀት እና በማዘመን፣ በሀገር ውስጥ እና በውጭ ትምህርታዊ፣ ሙያዊ እና ወታደራዊ ስልጠናዎች የመስጠት ሥራዎች መተግበራቸውም ተመላክቷል።
የተቋሙን ገፅታ መገንባት፣ የሙስና ወንጀሎችን መከላከል፣ ለደንበኞች ፍትሀዊ የዳኝነት አገልግሎት መስጠት፣ የስርዓተ- ፆታን ግንዛቤ ማሳደግ በአጠቃላይ ተቋሙ በተሰማራባቸው የስራ ዘርፎች አበረታች ውጤት መገኘቱ በውይይቱ ተገልጿል።
ከተወያዮች የተነሱ ሀሳቦችን እና ጥያቄዎችን መነሻ በማድረግ ማብራሪያ የሰጡት የመከላከያ ሚኒስትሯ ኢንጂነር አይሻ መሀመድ ባለፉት ዘጠኝ ወራቶች የተሠራው አጠቃላይ ሥራ ውጤታማና የሚበረታታ መሆኑን ገልፀው በአራተኛው ሩብ ዓመት ይበልጥ የተሻለ የእቅድ አፈፃፀም ውጤት ለማስመዝገብ ሁሉም ራሱን ዝግጁ ማድረግ እና መታተር እንደሚገባው አመላክተዋል።
ፈፃሚ አካላት የተቋሙን ታላላቅ ግቦች መሰረት ያደረገ የእቅድ አፈፃፀም ውጤት ሊኖራቸው እንደሚገባ
አሳስበው መከላከያ ታላቅ አቅም ያለው አንጋፋ ተቋም በመሆኑ ሙሉ አቅሙን ተጠቅሞ ወደ ውጤት ለመቀየር ከዚህ በላይ ጠንክሮ መስራት ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
በብርሃን እንዳየሁ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ዩቲዩብ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ቴሌግራም
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ፌስቡክ





