የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ሰኔ 28 ቀን 2017 ዓ.ም
የመከላከያ አዛዥነትና ስታፍ ኮሌጁ ያሰለጠናቸውን የ15ኛ ዙር የመደበኛ ኮርስ ከፍተኛ መኮንኖችን በድምቀት አስመርቋል።
በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ ንግግር ያደረጉት የመከላከያ ትምህርትና ስልጠና ዋና መምሪያ ሀላፊ ሌተናል ጀነራል ይመር መኮነን ኮሌጁ አንጋፋ የሀገራችንን ወታደራዊ አመራሮች በማፍራት የሀገር ባለውለታ ኮሌጅ መሆኑን ገልፀዋል።
ኮሌጁ ከሰባት ወዳጅ የአፍሪካ ሀገራት የመጡ አስራ ሶስት ከፍተኛ መኮንኖችን አሠልጥኖ ያስመረቀ መሆኑን ገልፀው ተመራቂዎች በቆይታቸው ከስልጠናው ጎን ለጎን የሀገራቸውን ባህል ለመለዋወጥ ችለዋል በወታደራዊ ዲፕሎማሲውም ውጤት አሥገኝተዋል።
ተመራቂ ከፍተኛ ወታደራዊ አመራሮቹ ያገኙትን ዕውቀት ወደተግባር በመለወጥ ውጤታማ ተግባራትን ለማከናወን የበለጠ ሊተጉ እንደሚገባም ሌተናል ጄኔራል ይመር መኮነን ገልፀዋል።
የሥልጠናውን ሪፖርት ያቀረቡት የኮሌጁ አዛዥ ብርጋዲየር ጀነራል ሙሉጌታ አምባቸው ኮሌጁ በመደበኛ መርሀ ግብር አሰልጥኖ ያስመረቃቸው ከፍተኛ መኮንኖች በዕውቀትና በክህሎት ብቁ መሆናቸው እና የኮሌጁን መስፈርት ማሟላታቸው ተረጋግጦ ለምረቃ መብቃታቸውን ተናግረዋል።
ስልጠናው በወታደራዊ አመራር ፤በብሄራዊ ደህንነት ጉዳዮች ፣ በውጊያና በጥምር ዘመቻ መስኩ ብቁ በሆኑ መምህራንና በተቋሙ ስትራቴጂክ አመራሮች መሰጠቱን ገልፀዋል።
የመከላከያ አዛዥነትና ስታፍ ኮሌጅ የሚሰጠውን የመማር ማስተማር በማዘመን በ2023 ከአፍሪካ ተመራጭ የአዛዥነትና የስታፍ መኮንኖች ማሰልጠኛ ማዕከል ለመሆን አቅዶ በርካታ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑ ይታወቃል ።
ዘጋቢ ብዙአየሁ ተሾመ





