የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ሃምሌ 18 ቀን 2017 ዓ.ም
የጦር ሃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ክቡር ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ በደቡብ ዕዝ ጠቅላይ መምሪያ ተገኝተው ከዕዙ ከፍተኛ አመራሮች ጋር ውይይት አድርገዋል።
ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ በየአቅጣጫው ነፍጥ እያነሱ ህዝባችንን ሰላም የሚነሱና ልማት የሚያደናቅፉ የሀገር ውስጥ ፅንፈኞች፣ የተፈጥሮ ሀብታችንን እንዳናለማና ጠንካራ ኢትዮጵያ እንዳትኖር የሚፈልጉ የውጭ ጠላቶቻችን ተላላኪና ጉዳይ አስፈፃሚ ባንዳ ናቸው ሲሉ ገልፀዋል።
ኢትዮጵያ በየጊዜው በሚፈጠሩ ሀገር ወዳድ አርበኞቿ ፀንታ የቆመች ናት ያሉት ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ፣ የአርበኞቻችንን ያክል ቁጥር ባይኖራቸውም የውስጥ ባንዳም ያልተለያት ሀገርም ናት ብለዋል።
አሁንም አገርን ለመበታተን እየተፍጨረጨሩ ያሉ የውጭ ተላላኪና ጉዳይ አስፈፃሚ ባንዳዎችን በመደምሰስ የሀገርን አንድነት ያስቀጠለው ሠራዊታችን የዚህ ዘመን አርበኛ ነው ሲሉ ተናግረዋል።
የውጭ ጠላቶቻችን ምንጊዜም የማይተኙልን በመሆናቸው፣ ሠራዊታችንን ጠንካራ፣ አስተማማኝና ግዳጁን በብቃት መፈፀም የሚችል አድርገን ገንብተነዋል ያሉት ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ በዚህ ሠራዊት ሀገርም እኔም እንኮራለን፣ እናንተም ክብር ይገባችኋል ብለዋል።





