የመከላከያ ሚኒስትር ኢንጅነር አይሻ መሀመድ አላጌ የጀግኖች አምባ እና ጊዜያዊ ማገገሚያ ማዕከል የሚገኙ የሀገር ባለውለታ የጦር ጉዳተኞችን በአካል ተገኝተው ያበረታቱ ሲሆን የተለያዩ የቁሳቁስ ድጋፎችን አድርገዋል። የምሳ ግብዣም አከናውነዋል።
በመከላከያ ኦርኬስትራ የሙዚቃ ዝግጅት በደመቀው መርሀ-ግብር ላይ ንግግር ያደረጉት የመከላከያ ሚኒስትር ኢንጅነር አይሻ መሀመድ ዘመኑን በዋጀ መልኩ በማሻሻል ታሪካዊ የሆነውን አላጌ የጀግኖች አምባ እና ጊዜያዊ ማገገሚያ ማእከል ወደተሻለ ደረጃ በማድረሱ ረገድ በቀጣይ ትልልቅ ስራዎች እንደሚሰሩ ገልጸው በርካቶች የሚማሩበት እና ዜጎች የሚኮሩበት ሆኖ እንዲቀጥል እንሰራለን ብለዋል።

ጀግንነት የትውልድ ቅብብሎሽ ነው ያሉት ኢንጅነር አይሻ መሀመድ አላጌ የጀግኖች አምባ እና ጊዜያዊ ማገገሚያ ማእከል የምትገኙ እናንተ የዚህ ዘመን ጀግኖች ናችሁ ሲሉም ገልፀዋል።
ኢንጅነር አይሻ መሀመድ የማዕከሉ መሬት በወረራ ከየ አቅጣጫው እየተሸነሸነ እንደሚገኝ ገልጸው የሚመለከተው የመንግስት አካል የራሱን እርምጃ እንዲወስድ ጠይቀዋል።
የመከላከያ ጤና ዋና መምሪያ ሀላፊ ሌተናል ጄነራል ጥጋቡ ይልማ በበኩላቸው የሀገራችንን ህልውና ለማረጋገጥ አካላችሁን አጉድላችሁ ጀግኖች ማዕከል መገኘት ትልቅ ክብር ነው ብለዋል።
ሀገር የምትቀጥለው ታሪኳን ማስቀጠል ሲቻል ነው ያሉት ሌተናል ጄኔራል ጥጋቡ ይልማ አባቶቻችን የጀመሩትን የጀግኖች አምባ እና ጊዜያዊ ማገገሚያ ማዕከል የተለያዩ እድሳቶች በማድረግ እና በተጠናከረ መልኩ ስራዎችን በማከናወን ታሪክ በማስቀጠል ላይ እንገኛለን ብለዋል።
ዘጋቢ ማርታ ግርማ
ፎቶግራፍ ደስታ ተረፈ





