በጄኔራል ፒየር ሺል የተመራ የፈረንሣይ ወታደራዊ ልዑክ ከኢፌዴሪ መከላከያ አመራሮች ጋር መክሯል። ምክክሩ የሁለቱን ሀገራት ወታደራዊ ትብብር ለማጠናከር ያለመ ሲሆን በቀጣይ በሚኖሩ የሠላም ማስከበር ኦፕሬሽኖችም ላይ አጠንጥኗል።
ወታደራዊ ትብብሩ የሁለቱ ሀገራት መሪዎች ያደረጓቸውን ስምምነቶች ተከትሎ የተደረገ እንደሆነም ነው የተመላከተው።

ኢትዮጵያ የቀጠናውን ሠላም ለማረጋገጥ እየሠራች ባለው ሥራ መደሰታቸውን የገለፁት የፈረንሣይ ምድር ኃይል አዛዥ ጄኔራል ፒየር ሺል በቀጣይነት አስፈላጊ በሆኑ ጉዳዮች በሁለትዮሽ ትብብር እንደሚሠሩ ገልፀዋል።
ጄነራል ፒየር ሺል በሠላም ማስከበር ተልዕኮ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ተሣትፎ አስፈላጊ ነው ተጠናክሮም መቀጠል አለበት ብለዋል።
ፈረንሣይ ለጋራ ተጠቃሚነት በወታደራዊ ቁሳቁስ ድጋፍ፣ በሠው ኃይል ሥልጠና እና ያልተቆራረጠ ወታደራዊ ትብብር ለማድረግ ዝግጁ መሆኗንም አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ ጦር በአፍሪካ ጠንካራ ኃይል መሆኑን የገለፁት የመከላከያ ትምህርትና ሥልጠና ዋና መምሪያ ኃላፊ ጄኔራል ይመር መኮንን ዘመኑ በሚጠይቀው ወታደራዊ ቴክኖሎጂ ታግዞ ግዳጅ ለመወጣት ከፈረንሣይ ጋር በትብብር እንሠራለን ብለዋል።

ጄኔራል ይመር መኮንን ከፈረንሣይ ጋር የረጅም ዓመታት ወታደራዊ ግንኙነት አለን ይህንኑ የቆየ ወዳጅነታችንን በተለያዩ ወታደራዊ ዘርፎች አጠናክረን መቀጠል እንፈልጋለን ብለዋል።
በውይይቱ የኢትዮጵያ መከላከያ ጄኔራል መኮንኖች ከፈረንሣይ መከላከያ ጋር መሠራት ባለባቸው ወታደራዊ መስኮች ከፈረንሣይ የጦር ልዑካኑ ጋር ሃሳብ ተለዋውጠዋል።
ሁለቱ ሐገራት በወታደራዊ መስክ ያላቸው ዳራ፣ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ሽብርተኝነት ለመዋጋት እያከናወናቸው ስላለው ተግባራት በመከላከያ ሠላም ማስከበር ማዕከል ገለፃ ተደርጓል።
ጄኔራል ፒየር ሺል በነገው ዕለትም ከጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ጋር ተገናኝተው እንደሚመክሩና ጉብኝት እንደሚያደርጉ ይጠበቃል።
ዘጋቢ ውብሸት አንበሴ
ፎቶግራፍ ተሰማ ኡርጌሳ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ድረ-ገፅ
https://dfmc.mod.gov.et/
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ዩቲዩብ
https://youtube.com/@fdredefenseforce-9629?si=Av-sDKCopw1FfTW2
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ቴሌግራም
https://t.me/+E_EOiTY9eq85ODI0
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ፌስቡክ
https://www.facebook.com/fdredefense.official





