ከቀናት በፊት በሁለትዮሽ ወታደራዊ ጉዳዮች ከኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ጄነራል መኮንኖች ጋር የመከሩት ጄነራል ፒየር ሺል የተለያዩ ተቋማትን ከጎበኙ በኋላ ከጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ጋርም ተወያይተዋል።
“ኢትዮጵያ የባህር በር በሰላማዊ መንገድ ለማግኘት ያላትን ፍላጎት እንዴት ይመለከታሉ?” በሚል ከመከላከያ ሚዲያ ጋዜጠኞች ለተነሳላቸው ጥያቄ ምላሽ የሰጡት የፈረንሣይ የምድር ኃይል አዛዥ ጄነራል ፒየር ሺል፤ “ኢትዮጵያ በጣም ትልቅ ሐገር ናት፣ በጣም ትልቅ የኢኮኖሚ ኃይልና ሕዝብም አላት፤ ስለዚህ ኢትዮጵያ የምትፈልጋቸውን ዕቃዎች መላክና ማስገባት እንድትችል ኢትዮጵያ የዓለም አቀፍ የንግድ መስመሮች አካል መሆን አለባት ብለዋል። እንደምታውቁት ፈረንሣይ መጥፎ ሐገር አይደለችም ይህ እንዲሳካ ፈረንሣይ የሰላም ድርድሩን እየደገፈች ነው የተባበሩት መንግስታትን ጨምሮ ብዙ ድርጅቶችንም በሃሳቡ እየደገፈች ነው” በማለት መልሰዋል።

“ከኢትዮጵያ ጋር የተካሄደው ወታደራዊ ትብብር ዋነኛ ዓላማ ምንድነው?” በሚል ለተነሳው ጥያቄም በሰጡት ምላሽ “እኔ የፈረንሣይ ሠራዊት መሪ ነኝ በጣም ትልቅና ጠንካራ ከሆነው ከኢትዮጵያ ሠራዊት ጋር ያለንን ትብብር ለማሻሻል አዲስ አበባ በመገኘቴ በጣም በጣም ኮርቻለሁ። ስለዚህ ትብብራችን በዋናነት የወታደራዊ ቁሳቁስ ድጋፍ ፣የሠላም ማስከበር ሥራዎች፣ የፈንጅ አወጋገድ ተግባራት ላይ፣ በሠው ኃይል ሥልጠና እና በሌሎችም ነው” ብለዋል።
ጄነራል ፒየር ሺል ኢትዮጵያ የቀጠናውን ደኅንነት ለማስጠበቅ ዋነኛ ተዋናይ መሆኗን ገልፀው፣ የቀጠናው ደኅንነት ሁኔታ እየተባባሰ በመሆኑ የኢትዮጵያ ተሳትፎ እጅግ አስፈላጊ መሆኑንና እንደ ፈረንሣይ ሠራዊት ተወካይ የኢትዮጵያን ሠራዊት እንደሚደግፉም አንስተዋል።
የኢትዮጵያን ሠራዊት ተሣትፎ በማድነቅ “ኢትዮጵያ በጣም ትልቅ ሐገር ናት፣ በጣም ጠንካራና ትልቅ ሠራዊትም አላት ከዚህ ሠራዊት ብዙ የምንማረው ነገር አለ ሲሉም አስረግጠው ተናግረዋል።
ከሰሞኑ በአዲስ አበባ የሚገኘው የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ዋናው መምሪያ የዓለም ኃያላንን ጨምሮ የተለያዩ ሐገራት የጦር መሪዎችን አስተናግዷል።





