በሜጄር ጄኔራል ሙሉጌታ ቡሊ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ጉብኝት ላይ የተገኙት የመከላከያ ሚኒስትር ክብርት ኢንጂነር አይሻ መሀመድ አንጋፋው ኮሌጅ ከዘመኑ ጋር የሚሄድ የሙያ ተቋምና ሀገራዊ አቅም እንዲሆን እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።
ኮሌጁ ዘመኑ የደረሰበት ደረጃ ለመድረስ ራሱን ማዘጋጀት እንደሚገባው የገለፁት ሚኒስትሯ የስራ ፈጠራን ከሃሳብ እስከ ውጤት በተቋሙ ኢንዱስትሪዎችና ወደ ምርት የሚለወጡበትን ዕድል ማመቻቸት እንደሚገባም ተናግረዋል።

የተቋሙን ባህሪና ሁኔታ የተረዱ ባለሙያዎችን ማፍራት ወሳኝ መሆኑን የጠቆሙት ሚኒስትሯ በተለይም በግንባታ ፤ በፊኒሽንግና በዲዛይን ባለሙያዎችን ማፍራት ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባም ጠቁመዋል።
የመከላከያ ትምህርትና ስልጠና ዋና መምሪያ ሀላፊ ጀኔራል ይመር መኮንን በበኩላቸው ፣ሰራዊቱን በቴክኖሎጂና በሰው ሀይል ለማዘመን ከተያዘው ዕቅድ አንፃር ኮሌጁን ዘመኑ የደረሰበት ደረጃ ለማድረስ በርካታ ስራዎች እየተሰሩ እንደሚገኙ ገልፀዋል።
የመከላከያ ኢንተርፕረነርሺፕና ኢኖቬሽን ማዕከልን ከኮሌጁ ጋር ማስተሳሰር አዋጭ በመሆኑም በጋራ የሚሰሩበት ሁኔታ እየተመቻቸም እንደሚገኝ ጠቁመዋል።

በኮሌጁ ያሉ አቅሞችን በመጠቀም ለውጊያ አቅም የሆኑ ሙያተኞችን በማፍራት፣ የተለያዩ የተሽከርካሪና የጦር መሳሪያ መለዋወጫን ከማምረት ባለፈ ለተቋሙ ለሀገርና ለአካባቢው ማህበረሰብ ጥቅም እንዲሰጥ እየተሰራ እንደሚገኝም ጠቁመዋል።
በኮሌጁ የተገኙ ለውጦችን በማጠናከርና ለፈጠራ ትኩረት በመስጠት ለተቋሙ ተልዕኮ አጋዥ ሁኔታ ለመፍጠር ጥረቶች እየተደረጉ እንደሚገኙም ተናግረዋል።
ዘጋቢ ብዙአየሁ ተሾመ
ፎቶግራፍ ገነት አወቀ





