የጦር ኃይሎች ኮምፕሬሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ለሀገር ባለውለታ ለሆኑ የሰራዊት አባላትና ቤተሰቦቻቸው የሚሰጠውን የሕክምና አገልግሎት ይበልጥ በማዘመን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ የዳሌ አጥንት ሙሉ መገጣጠሚያ ቅየራ (Total Hip Replacement) ቀዶ ጥገና በይፋ መጀመሩን አስታውቋል።
ዘመናዊ የጤና ቴክኖሎጂ ለጀግኖቻችን በሚል መሪ ቃል በተካሄደው በዚህ የማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይ ከፍተኛ አመራሮችና የዘርፉ ባለሙያዎች ተገኝተዋል።

ሆስፒታሉ ለረጅም ዓመታት በዕውቀት ምንጭነቱ ታላላቅ ባለሙያዎችን ማፍራቱን ያወሱት የሆስፒታሉ አዝዥ ሜጄር ጄነራል ዶክተር ኃይሉ እንደሻው ሆስፒታሉ ከሚሰጣቸው ዘርፈ ብዙ የቀዶ ጥገና አገልግሎቶችን በማስፋፋት ራሱን እያዘመነ ይገኛል ብለዋል።
ይህ የዳሌ አጥንት ቅየራ አገልግሎት መጀመሩም ለሰራዊቱ ያለውን ሰፊ ፍላጎት ለማሟላት ትልቅ አቅም ይፈጥራል ያሉት ጄነራል መኮንኑ በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ ለተከናወነው የዳሌ መገጣጠም ተግባር የተሳካ የህክምና አገልግሎት ተግባር አመስግነዋል።
ሰራዊታችን ለሀገር በሚከፍለው መስዋዕትነት የሚመጥን የሕክምና አገልግሎት እየሰጠን እንገኛለን ያሉት የሆስፒታሉ ቺፍ ክሊኒክ ዳይሬክተር ብርጋዲየር ጄነራል ዶክተር ገነት ይማም አሁን ደግሞ አገልግሎቱን ከፍ በማድረግ የዳሌ አጥንት መገጣጠሚያ ችግር ለደረሰባቸው ጀግኖቻችን ፍቱን መፍትሄ መስጠት መጀመራችን ትልቅ ስኬት ነው ብለዋል።

ይህ ሕክምና ከፍተኛ ወጪና አቅምን የሚጠይቅ ነው ያሉት የአጥንትና መገጣጠሚያ ቀዶ ሕክምና ስፔሻሊስት ዶክተር ተሾመ ጠና አሁን በሆስፒታላችን መጀመሩ ተረጂዎች ያለ ህመም በቀላሉ ወደ ቀድሞ ጤንነታቸው እንዲመለሱ ያስችላል ሲሉ ገልፀዋል።
የዋሺንግተን ዲሲ ሆስፒታል ባለቤትና የኢትዮጵያ ጤና እንክብካቤ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ዶክተር ማርቆስ ፈለቀ እና የጤና ሚኒስቴር ተወካይ ዶክተር ኤርሜያስ ሙላቱ በበኩላቸው የተቋሙን ጅምር በማድነቅ ልምዳቸውንና አስፈላጊውን ድጋፍ ለማድረግ ቁርጠኝነታቸውን ገልጸዋል።
በመርሃ ግብሩ የታደሙት ሙያተኞች የዳሌ መገጣጠም ተግባር የተደረገላቸውን ታካሚዎች የመጎብኘትና የአገልግሎት አሰጣጥ ሂደቱን ተዘዋውረው ተመልክተዋል።





