በምረቃ ስነ-ስርዓቱ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የመከላከያ ሰላም ማስከበር ማዕከል ኃላፊ ሜጀር ጀኔራል አዳምነህ መንግስቴ ታሪካዊ ጠላቶቻችን አሁንም የሀገራችንን ሠላም በመነሳት ልማት እና ዕድገታችን ለማደናቀፍ ቢጥሩም በህዝቡ እና በሠራዊቱ ጥንካሬ ህልማቸው እየከሸፈ ይገኛል ብለዋል።

የኢትዮጵያ ሠራዊት የሀገሩን ሰላም ከማፅናት አልፎ የጎረቤት አገራትን ሰላም ለማረጋገጥ በተባበሩት መንግስታት እና በአፍሪካ ህብረት ተልዕኮዎችን በመወጣት በግንባር ቀደም የሚታወቅ ሠራዊት ያላት መሆኑን ተናግረዋል።
የመሠረታዊ ውትድርናን ሥልጠናን በአግባቡ የተወጡ ተመራቂ ምልምል ወታደሮች በቀጣይ የሚሰጣቸውን ስልጠና በጠንካራ ዲሲፕሊን በመከታተል መድረስ ከሚገባቸው ደረጃ መድረስ እንደሚገባቸው አሥገንዝበዋል።

የሁርሶ ኮንቲንጀንት ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት አዛዥ ብርጋዲየር ጀኔራል አዲሱ ተርፋሳ በበኩላቸው ሃገራችን አሁን ላይ ውስብስብ ፈተናዎችን እየተሻገረች የልማት ግቦቿን እያሳካች እንደምትገኝ ገልፀው ሠላሟን የሚያረጋግጡ ወታደሮቿ ሆናችሁ በመመረቃችሁ ልትደሰቱ ይገባል ብለዋል።

ተመራቂዎች በስርዓተ ትምህርቱ (በካሪኩለም) መሠረት ሁሉምንም የመሠረታዊ ውትድርና ሥልጠናቸውን በተሟላ ሁኔታ በተግባር ልምምድ እና በቲዎሪ መውሰዳቸውን ተናግረው የቀሰሙትን አቅም በተግባር ማዋል እና ለሚሸጋገሩበት ቀጣይ ሥልጠና ዝግጁ መሆን እንደሚጠበቅባቸው አሥገንዝበዋል።





