የመከላከያ ሎጂስቲክስ ዋና መምሪያ ሙሉ ዕድሳትና ሙከራ ያደረገላቸውን በርካታ የሜካናይዝድ ትጥቆችን ወደሀይል አስገብቷል።
በዝግጅቱ ላይ በመገኘት ትጥቆቹን የጎበኙት የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ክቡር ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ በተሰሩት ስራዎች መደሰታቸውን ገልፀው ፣የዋና መምሪያውና የጥገና ማዕከሉ አመራር ፤ ባለሙያና አባላቶች ተአምር የሚባል ስራ መስራታቸውን ገልፀዋል።

ዋና መምሪያው ሀገርን በቢሊየን ከሚቆጠር ወጪ ከማዳኑ ባለፈ በራስ አቅምና ፈጠራን በማሻሻል ተአምራዊ የሚባል ስራ መስራት እንደምንችልም ያሳየ ነው ብለዋል።
ለረጅም ዓመታት ተጥለው የነበሩና አረም ወርሷቸው የቆዩትን በርካታ የሀገር ሀብቶችን ሙሉ እድሳትና ሙከራ ተደርጎባቸው ወደ ሀይል መግባታቸው የሰራዊቱን የውጊያ ዝግጁነት በከፍተኛ ሁኔታ ያሳድጉታል ሲሉም ገልፀዋል።
ትጥቆቹ የሰራዊታችንን የውጊያ አቅም የሚያሳድጉና ተቀብሮ የነበረ ሀገራዊ ሀብትን ወደ ጥቅም የዋለበት ብቻ ሳይሆን የመከላከያ የሎጂስቲክስ ዋና መምሪያ የደረሰበትን ደረጃም ያሳየ መሆኑን ጠቁመዋል።

ተቋሙ ባስቀመጠው አቅጣጫ መሠረት ውጤታማ ተግባራትን ላከናወኑ የዋና መምሪያው አመራሮች ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
ሎጂስቲክስ ዋና መምሪያ በሰፈረባቸው ቦታዎች የአካባቢውን መሠረት ልማት በማልማትና ለሰራተኛው ምቹ የስራ አካባቢ የመፍጠር እንቅስቃሴው ለውጤታማነቱ ያለው ሚናም ወሳኝ በመሆኑ ሊቀጥል እንደሚገባም አሳስበዋል።

የተጀመሩ የዕድሳትና የፈጠራ ስራዎችን አጠናክሮ በማስቀጠል ለሀገር እና ለተቋም ጥቅም እንዲውሉ የማድረግ ጥረቱ ተጠናክሮ እንዲቀጥልም አሳስበዋል።
በመከላከያ የሎጂስቲክስ ዋና መምሪያ ጥገናና ሙከራ ያደረገባቸውና ውጤታማነታቸው የተረጋገጡት ትጥቆችን ለመከላከያ የሜካናይዝድ ዕዝ አስረክቧል።
በዝግጅቱ ላይ የጦር ሀይሎች ምክትል ኤታማዦር ሹም ጀነራል አበባው ታደሰን ጨምሮ ከፍተኛ የሰራዊቱ አመራሮች ተገኝተዋል።





