በትግራይ ክልል በተሃድሶ ሥልጠና (DDR) ሂደት ያለፉ፣ የቀድሞ የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት አባላት የመልሶ ማቋቋም የውይይት መድረክ በአዲስ አበባ ተካሂዷል።
በውይይት መርሃ ግብሩ የብሔራዊ ተሃድሶ ኮሚሽን፣ በሀገሪቱ በተለያዩ ክልሎች ሲንቀሳቀሱ የነበሩ የቀድሞ ተዋጊዎችን ዲሞብላይዝ በማድረግ፣ የተሃድሶ ስልጠና በመስጠትና መልሶ በማቋቋም ወደ ሰላማዊ ህይወት እንዲመለሱ የማድረግ (DDR) እንዲሁም የሰላምና የልማት አጋር እንዲሆኑ እየሰራ መሆኑ ተገልጿል።

በሰሜኑ ጦርነት ህወሃትን በመደገፍ በጦርነቱ የተሳተፉ የቀድሞ የኢፌዴሪ መከላከያ ሰራዊት ከፍተኛ አመራርና አባላት የነበሩ እንዲሁም በአለም አቀፍ የሰላም ማስከበር ላይ የነበሩ የቀድሞ ተዋጊዎች ውስጥ 500 ያህሉ በDDR ፕሮግራም ሂደት ማለፋቸው የተገለፀ ሲሆን በሠራዊቱ መተዳደሪያ ደንብ መሠረት ጥቅማጥቅም ማግኘት የሚችሉበት አሠራር መዘርጋቱም ተጠቁሟል።
በምክክር መድረኩ ላይ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት የመከላከያ የሰው ሃብት አመራር ዋና መምሪያ ኃላፊ ሌተናል ጄነራል አጫሉ ሸለመ እንደገለፁት የሠላም መንገድ ሁሌም የሚያዋጣ በመሆኑ አሁንም ታጥቀው የሚንቀሳቀሱ ኃይሎች ወደ ውይይትና ሠላም መምጣት አለባቸው።
ተቋሙ ለዘላቂ ሰላም ሲባል የቀድሞ ተዋጊዎች በተቋሙ አሠራር እና መመሪያ መሠረት መልሶ የማቋቋም ሥራዎች እንደሚከናወኑም ጄኔራል መኮንኑ ገልፀዋል።

ኢትዮጵያ ባለፋት ጊዜያት አውዳሚ በሆኑ ጦርነቶች ውስጥ ማለፏን ያነሱት የብሔራዊ ተሃድሶ ኮሚሽን ኮሚሽነር ተመስገን ጥላሁን በርካታ የታጠቁ ኃይሎች ትጥቅ እየፈቱ መሆናቸውንና ኮሚሽኑ አሰልጥኖ ወደ ሠላማዊ ሕይወት እየመለሳቸው መሆኑን ገልፀዋል።
ከ371 ሺህ በላይ የታጠቁ ኃይሎች በአገሪቱ በተለያዩ አካባቢዎች መኖራቸውንና ከነዚህም ውስጥ 80 ሺህ ያህሉን በተሃድሶ ሥልጠና ወደ ማህበረሰቡ ማምጣት መቻሉን ያወሱት የብሔራዊ ተሃድሶ ኮሚሽን ምክትል
ኮሚሽነር ብርጋዲየር ጄነራል ደርቤ መኩሪያ ከመከላከያ ሠራዊቱ ወጥተው በሌላ ጎራ ከተሰለፋት ከ5 ሺህ ሁለት መቶ አባላት ውስጥ 5 መቶ ያህሉ በተሃድሶ ሥልጠና ማለፋቸውን ተናግረዋል።
ምክትል ኮሚሽነሩ በተለያዩ ተቋማት ውስጥ ሲሰሩ የቆዩና ጦርነት ውስጥ ተሣትፈው የነበሩ ወጣቶች በተሃድሶ ሥልጠና(DDR) ካለፉ ከተቋማቱ ጋር በመነጋገር ተመልሰው ወደ ሥራ የሚገቡበት አሠራር መመቻቸቱንም ገልፀዋል።





