“የኤሌክትሮማግኔቲክ ስፔክትረም ልዕልና ለሀገር ሉዓላዊነት” በሚል መሪ ቃል የመጀመሪያው ሀገራዊ የኤሌክትሮኒክስ ዋርፌር ወርክሾፕ ተካሂዷል።

በዝግጅቱ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ክቡር ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ ፣በዘመናዊ ውጊያ የህልውና ጉዳይ በሆነው የኤሌክትሮኒክስ ዋርፌር መስኩን ለማላቅና ሀገራዊ አቅም ለማድረግ በርካታ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ገልፀዋል።
ከምድር ፣ከባህር፣ ከአየር ሀይልና ከሳይበር በተጨማሪ የኤሌክትሮኒክስ ስፔክትረሙን ልዕልና በማረጋገጥ ለሀገራዊ ሉዓላዊነት ለማዋል ብቃት ያለው የሰው ሀይል፣ ዘመኑን የዋጁ ትጥቆችን ለመታጠቅ ተቋሙ በትኩረት አየሰራ እንደሚገኝ ለዚህም ሀገራችን እየተገበረች ያለችውና ከፍተኛ ውጤት የተመዘገበበት የዲጅታል ኢትዮጵያ 2030 አካል ሊሆን ይገባል ብለዋል።

ተበታትነው ያሉ ሀገራዊ አቅሞችን በማሰባሰብ መስራትና በራስ አቅም ለማምረት እንደሚገባም አሳስበዋል።
ወርክሾፑ ወቅታዊና አስፈላጊ መሆኑን ገልፀው ፣በዘርፉ ያለንን ልምድ በመቀመርና ከዘመኑ ቴክኖሎጂ ጋር ለመራመድ ፅኑ መሰረትን የጣለና ታሪካዊ ነው ብለዋል።
የብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ዳይሬክተር ጀነራል አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን ፤ ተለዋዋጭ በሆነው የአለማችን ሁኔታ የቴክኖሎጂ የበላይነት ያለውና ስፔክትረሙን የሚቆጣጠር ሀይል ነገሮችን እንደሚቆጣጠር ታሪክንና ወቅታዊ የአለምን ሁኔታ ተንተርሰው አብራርተዋል።

የሀገራችን እውነተኛ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በዘርፉ ተወዳዳሪ መሆን ሲቻል ብቻ በመሆኑ እየተሰሩ ያሉት ስራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ አስገንዝበዋል።
በዕለቱም የኢመደአ ዋና ዳይሬክተር ወይዘሮ ትዕግስት ሃሚድ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት አሥተላልፈዋል።

በዝግጅቱ ላይ የኢመደአ ዋና ዳይሬክተር ወይዘሮ ትዕግስት ሃሚድን ጨምሮ የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገብረሚካሄል ፣ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሀላፊዎች ፤ የሰራዊቱ የፀጥታና የደህንነት አመራሮችና የዘርፉ ምሁራን ተሳታፊ ሆነዋል።
ዘጋቢ ብዙአየሁ ተሾመ
ፎቶግራፍ ገነት አወቀ





